“የፋይዳ መታወቂያ ፕሮጀክት ስኬትማ እንዲኾን የመሪዎችን ቁርጠኝነት እና ድጋፍ ይጠይቃል” አብዱ ሁሴን (ዶ.ር)

5
ደሴ፡ ሚያዚያ 28/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የፋይዳ መታወቂያ ፕሮጀክት ተግባር በስኬት እንዲጠናቀቅ የመሪዎች ቁርጠኝነት እና ድጋፍ ወሳኝ መኾኑን የአማራ ክልል ምክትል ርእሰ መሥተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ.ር) ገልጸዋል።
የፋይዳ መታወቂያ ሕገ ወጥነትን እና ወንጀሎችን ለመከላከል ያለው ጠቀሜታ የጎላ ነው ብለዋል። በተለይም ግለሰቦች ማንነታቸውን ደብቀው ወንጀል የመሥራት ዕድላቸውን የሚያስቀር መኾኑን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቱ በሀገር ደረጃ እንደ ቁልፍ ተግባር የሚወሰድ እና በሁሉም ተቋማት የተቀላጠፈ አገልግሎት እንዲሰፍን የሚረዳ በመኾኑ ፋይዳውን በሚገባ በመረዳት በአጭር ጊዜ ውስጥ መተግበር እንደሚገባ አሳስበዋል።
የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ዮዳሄ አርዓያሥላሴ በኢትዮጵያ የፋይዳ መታወቂያ ምዝገባ ከ43 ሚሊዮን በላይ መሻገሩን አስታውቀዋል። አሁን ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ ያለው በገጠሩ አካባቢ በግብርና ሥራ በተሰማሩ ዜጎች ላይ መኾኑንም አመላክተዋል።
የተለያዩ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት የፋይዳ መታወቂያን እንደ ቅድመ-ሁኔታ የመጠየቅ በአዋጅ የተደነገገ መብት እንዳላቸው የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ እንደ ጤና፣ ግብርና፣ ቴሌኮም፣ ንግድ እና ገቢዎች ያሉ ዘርፎች አገልግሎታቸውን ከመታወቂያው ጋር እያያያዙት መኾኑን ገልጸዋል።
የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የምዝገባ አስተባባሪ ደጀን ገብሬ እንደገለጹት ዲጂታል መታወቂያው ኢኮኖሚን በማስተሳሰር ረገድ ትልቅ ሚና አለው።
በተለይም፦
👉የባንክ አገልግሎትን ለማዘመን እና ደኅንነቱን ለማረጋገጥ ይረዳል።
👉ቁልፍ የልማት ፕሮግራሞችን እርስ በእርስ ለማቀናጀት እንደ ድልድይ ያገለግላል ነው ያሉት።
የደቡብ ወሎ ዞን ምክትል አሥተዳዳሪ አሊ ይማም በዞኑ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ እንዲወስዱ መደረጉን ገልጸዋል። ይህ ውጤት ሊመዘገብ የቻለውም መሪዎች ለሥራው ትኩረት ሰጥተው በቁርጠኝነት በመንቀሳቀሳቸው መኾኑን አንስተዋል።
የፋይዳ መታወቂያ የዜጎችን ማንነት በዲጂታል መንገድ በማረጋገጥ፣ ለአስተማማኝ ደኅንነት እና ለተፋጠነ ሀገራዊ ዕድገት መሠረት እየጣለ መኾኑም በመድረኩ ተመላክቷል።
ዘጋቢ፦ ሳሙኤል ኪሮስ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !
Previous articleየመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቀዳማይ ልጅነት ልማት ጉባኤ በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው።
Next articleየሀገር ውስጥ ምርት መበራከት አቅርቦት እና ፍላጎት እንዲመጣጠን ያደርጋል።