ያልተረጋገጠ መረጃ ጥፋት

4
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 13/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በማኅበራዊ ሚዲያ አማካኝነት በርካታ መረጃዎችን በፍጥነት ማግኘት ይቻላል። ነገር ግን ከዚሁ ጋር ተይዞ ከሚመጣው ሀሰተኛ መረጃ (Fake News) ጋር መታገል የወቅቱ ትልቅ ፈተና ኾኗል።
✍️መረጃ እንዴት አሳሳች ኾኖ ይሠራጫል?
👉አሳሳች መረጃ (Disinformation)፦
ሀሰት መኾኑ እየታወቀ ሰዎችን ለማታለል በታቀደ እና ኾን ተብሎ የሚሠራጭ ሀሰተኛ መረጃ ነው።
👉የተሳሳተ መረጃ (Misinformation)፦
መረጃው የተሳሳተ ኾኖ የሚያሠራጨው አካል ግን እውነት መስሎት ወይም ትክክል መኾኑን አምኖበት (ያለ ተንኮል ዓላማ) የሚያሠራጨው መረጃ ነው።
👉በእውነት ላይ የተመሰረተ ጎጂ መረጃ (Mal information)፦ መረጃው በራሱ እውነት ወይም ከእውነተኛ ሁነቶች የተወሰደ ነው።
መረጃውን ለመግለጥ የተፈለገበት ዋና ዓላማ ደግሞ በአንድ ግለሰብ፣ ድርጅት ወይም ሀገር ላይ ኾን ብሎ ጉዳት ለማድረስ ተብሎ የሚሠራጭ ነው።
✍️በቅርቡ የተከሰቱ የሀሰተኛ መረጃ ጥፋት ማሳያዎች
#የምያንማር ተሞክሮ (የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መረጃ) እ.ኤ.አ. በ2017 በምያንማር በተከሰተው ቀውስ ላይ ጥልቅ ምርመራ ያካሄዱት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (UN) የሰብአዊ መብት ባለሙያዎች የፌስቡክ ማኅበራዊ ሚዲያ በሀገሪቱ የጥላቻ ንግግር እንዲዛመት ከፍተኛ ሚና መጫወቱን ይፋ አድርገዋል።
በማኅበራዊ ሚዲያ በተሠራጩ የጥላቻ ንግግሮች ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹሃን ተገድለዋል፤ መንደሮች ተቃጥለዋል፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ተፈናቅለዋል።
#የደቡብ አፍሪካ ተሞክሮ፦ በደቡብ አፍሪካ የተዛመቱ ሀሰተኛ መረጃዎች በውጭ ዜጎች ላይ የጥላቻ ማዕበል ማስከተላቸውን የቪኦኤ (VOA) እንግሊዘኛ ክፍል ዘግቧል። የመረጃ ማረጋገጫ ተቋም የኾነው አፍሪካ ቼክ (Africa Check) እንዳመለከተው ደግሞ የስደተኞች ቁጥር ተጋንኖ ቀርቧል።
​የውጭ ዜጎች የሀገሪቱን የሥራ እድል ሙሉ በሙሉ ወስደዋል እንዲኹም የእስር ቤቶች አብዛኞቹ እስረኞች የውጭ ዜጎች ናቸው የሚሉ ያለበቂ ማስረጃ የተሠራጩ ወሬዎች ጥቃቱ እንዲባባስ አድርጎታል።
​በዚህም ምክንያት የመንጋ ጥቃቶች ተቀስቅሰው የብዙ ስደተኞች ሱቆች ተዘርፈዋል፣ ተቃጥለዋል። ስደተኞች ንብረታቸውን ጥለው ለመሰደድ ተገድደዋል። ሀገሪቱ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አበላሽቶታል።
✍️ማንኛውንም መረጃ ከማጋራት በፊት በጥርጣሬ መመልከት፣ በስሜት ከመመራት ይልቅ እውነት መኾኑን ከአስተማማኝ የመረጃ ምንጮች ማረጋገጥ እና የተረጋገጡ የመረጃ ሥርጭቶችን ብቻ መጠቀም ተገቢ መኾኑን አይርሱ።
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይኹኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous articleከንቱ ምኞት ያነገበው ጥምረት እና ተደጋጋሚ ስህተቱ