
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች በደጀን ኀይል ተመልምለው ”በጀግንነት መጠበቅ በሰብዓዊነት ማገልገል” በሚል መሪ ሀሳብ ለተከታታይ ጊዚያት ሥልጠና ሲከታተሉ የቆዩ የጸጥታ አባላት ተመርቀዋል።
የአማራ ክልል ሚሊሻ ኮሚሽን ኮሚሽነር አስቻለ አላምሬ ፤ በሥልጠና ቆይታችሁ ያገኛቹሁትን እውቀት ተጠቅማቹሁና ለሕዝባቹሁ ጋሻና መከታ ሆናችሁ ለፍትሕ፣ ለሰላምና ለሕዝብ ክብር ልትቆሙ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።
ሕዝብ ያመነው ኃይል መቼም ቢሆን ድል ያደርጋል ያሉት ኮሚሽነሩ ከሥልጠና ማግስት ወደ መጣቹሁበት አካባቢ ስትመለሱ የእርስ በርስ አንድነታቹሁን በማጠናከርና ሰላምን በማረጋገጥ ሕዝባችሁን በፅናት ልታገለግሉ ይገባል ብለዋል።
በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የአማራ ክልል ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኮሚሽነር ደጀኔ ልመንህ ፤ በሥልጠና ቆይታችሁ ያገኛቹሁትን የውጊያና የአመለካከት ክህሎት ለዞኑ ሕዝብ ትልቅ አቅም ነው ብለዋል።
በመሆኑም በየአካባቢያችሁ የሕግ የበላይነትን በማስከበርና የዞናቹሁን ሰላም በማረጋገጥ ሕዝባችሁን በታማኝነት ማገልገል ይገባቹሀል ብለዋል።
የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አወቀ አስፈሬ ፤ ባለፉት ጊዚያት የጸጥታ አካላት ከኅብረተሰቡ ጋር በቅንጅት በመሥራት በዞኑ አንፃራዊ ሰላም ማስገኘት ተችሏል ብለዋል። የዞኑ አስተዳደር አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል።
በመጨረሻም ሥልጠናው በስኬት እንዲጠናቀቅ ያደረጉ አካላትን አመስግነዋል።
በተያያዘም የዞኑ ሰላምና ጸጥታ መምርያ ኃላፊ አንተነህ ታደሰ በስልጠናው ያገኛቹህትን ክህሎት ተጠቅማቹህ ሰላም ወዳዱን የዞናችንን ሕዝብ ሰላም ልታረጋግጡ ይገባል ብለዋል።
በስነስርዓቱ በስልጠና ወቅት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅናና ሽልማት ተሰጥቷል። መረጃው የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ኮሙኒኬሽን ነው።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
