
በመላው ኢትዮጵያ እየተካሄደ በሚገኘው የአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል መርሐ ግብር ላይ እስከ ቀኑ 9 ሰዓት ድረስ ብቻ 700 ሚሊዮን ችግኞች መተከላቸውን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ አስታወቁ።
ሚኒስትሯ የዕለቱን የችግኝ ተከላ አፈጻጸም አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፣ ኢትዮጵያውያን የያዙትን 800 ሚሊዮን ችግኞችን በአንድ ጀምበር የመትከል ሀገራዊ ግብ ለማሳካት በከፍተኛ የሀገር ፍቅር ስሜት እና ንቃት እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል።
በዚህም መሠረት ከማለዳው ጀምሮ እስከ ቀኑ 9 ሰዓት ባለው ጊዜ 22.2 ሚሊዮን ዜጎች በዕለቱ መርሐ ግብር ላይ በንቃት በመሳተፍ አረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል ነው ያሉት።
በተሰበሰበው መረጃ መሠረትም 256 ሺህ ሄክታር መሬት በችግኝ መሸፈን እንደተቻለ ሚኒስትሯ አብራርተዋል።
ይህ አሃዝ የሚያሳየው ሕዝቡ በአንድ ጀምበር ለመትከል ካቀደው የ800 ሚሊዮን ችግኝ ተከላ ግብ መዳረሻ ላይ እጅግ መቃረቡን ነው ብለዋል።
በቀሪዎቹ የከሰዓት በኋላ ሰዓታት መርሐ ግብሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የተገለጸ ሲሆን፣ አጠቃላይ የዕለቱ የችግኝ ተከላ የዋና አፈጻጸም መረጃዎች በቀጣይ ተጠናቅረው ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረጉ ይጠበቃል።
አሁን ላይ ያለው ከፍተኛ መነሳሳት ኢትዮጵያ በአንድ ጀምበር ያቀደችውን ግብ ልታሳካ እንደምትችል ትልቅ ማሳያ መሆኑም ተመላክቷል።
