
ኢትዮጵያ ለዘመናት ጸንታ የቆመችው በበጎ እና በክፉ ቀናት ተደጋገፎ ባሳለፈው የሕዝቧ ጠንካራ ማኅበራዊ እና መንፈሳዊ እሴት አማካኝነት ነው። እነዚህን ለዘመናት ሀገርን እና ሕዝብን አስተሳስረው ያቆዩ የሰላም እሴቶችን በቃላት ከማስተማር ባሻገር “በተግባር ኖሮ ለሌሎች ምሳሌ መኾን” እንደሚገባ በአማራ ክልል የሚገኙ የሃይማኖት አባቶች አሳስበዋል።
የሃይማኖት አባቶችም መጽሐፉ የሚለውን ሳይሸራረፉ ማስተማር ብቻ ሳይኾን እኔ ኾኜ አሳይቼ ነው መናገር ያለብኝ በሚለው መርሕ በፍቅር እና በታማኝነት ለአማኞች ምሳሌ መኾን ይገባቸዋል ብለዋል።
የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አማካሪ ሼህ ጀውሃር መሐመድ በሃይማኖት መሪዎች ላይ ሰላም ፈላጊነት፣ ታማኝነት እና ሀቀኝነት ጎልቶ መታየት ወሳኝ መኾኑን ገልጸዋል። የሃይማኖት ተቋማት ለሰላም ትልቅ ኀላፊነት አለባቸው፤ የመጀመሪያው ተግባራቸው አማኞቻቸው በሚገኙበት ቦታ ሁሉ የሰላም እና የሥነ ምግባር ትምህርት ማድረስ ነው ብለዋል።
የሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ዋና ጸሐፊ መጋቢ ደሳለኝ አባተ የእርቅ እና የአብሮነት እሴቶቻችንን የምናስቀጥላቸው ከውጭ ኾነን በመመልከት ሳይኾን አብሮ ኾኖ በማጋራት እና በመተግበር ነው ብለዋል። የሃይማኖት ተቋማት እና መሪዎች ለሰላም እሴቶች ፍሬያማነት ቀዳሚ ኾነው ሊሠሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
እሴቶችን ማደስ እና የቆዩትን የእርቅ፣ ሽምግልና እና የመረዳዳት እሴቶች ከወቅቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማጣጣም ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ያስፈልጋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
