በአማራ ክልል የማይበገር የጤና ሥርዓት ለመገንባት እየተሠሩ ያሉት ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው።

9
🩺የአማራ ክልል ጤና ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ አካሂዷል።
የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አብዱልከሪም መንግሥቱ የማይበገር የጤና ሥርዓት ለመገንባት ከቢሮው እስከ ታችኛው መዋቅር ድረስ የተሠራው ሥራ ውጤታማ እንደነበር ገልጸዋል።
🏥በየወረዳዎች የማኅበረሰብ አቀፍ መድኃኒት ቤቶችን ለማዳረስ የተጀመረው ዕቅድ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ተግባርን አቀናጅቶ በመምራት፣ የተደራጀ ክትትል እና የድጋፍ ሥርዓትን ተግባራዊ ማድረግ፣ ሞዴል የጤና ተቋማትን በመፍጠር፣ ኅብረተሰቡን ያሳተፈ የጤና አገልግሎት ሥርዓቶች ውጤታማ መኾናቸውን ገልጸዋል።
በ2018 በጀት ዓመት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማስፋት ክፍተቶችን አርሞ በ2019 በጀት ዓመት የተሻለ ለመፈጸም መዘጋጀት እንደሚገባም አሳስበዋል።
የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ጤና መምሪያ ኀላፊ ሰኢድ የሻው 27 የሚኾኑ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ የከተማ አሥተዳደሩን ጤና ጣብያዎች ደረጃ ለማሻሻል ጥረት መደረጉን አንስተዋል።
🔬💻 የወረቀት አልባ የጤና መረጃ አገልግሎት ሥርዓት ተግባራዊ እየተደረገ መኾኑን ተናግረዋል። ማኅበረሰቡን በማሳተፍ፣ ጠንካራ ክትትል እና የድጋፍ ሥርዓት በመዘርጋቱ የተሻለ አፈጻጸም ማምጣት እንደተቻለም ተናግረዋል።
የምሥራቅ ጎጃም ዞን ጤና መምሪያ ኀላፊ የሽዋስ አንዱዓለም በ84 ጤና ጣቢያዎች መሳሪያ በማሟላት የአልትራ ሳውንድ ምርመራ አገልግሎት መስጠት መቻሉን አንስተዋል።
በሁሉም ወረዳዎች ላይ የማኅበረሰብ አቀፍ መድኃኒት ቤቶችን ለማስፋፋት ታቅዶ በ15 ወረዳዎች ወደ ሥራ ማስገባት ተችሏል። በቀጣይም በጤና ተቋማት የዲጂታላይዜሽን ሥርዓትን ተገባራዊ ለማድረግ ትኩረት እንደሚሰጥም ጠቁመዋል።📲🌐
🏆በበጀት ዓመቱ የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የጤና መምሪያዎች፣ የጤና ተቋማት እና ግለሰቦችም ዕውቅና ተሰጥቷል።
ዘጋቢ:- አሰፋ ልጥገበው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous article
Next articleየመከሩ በሰላም ብዕር እና ብራና የተጻፈ ታሪክ ለልጆቻቸው አስረክበዋል።