
እንግዳ ተቀባይ፤ ሃይማኖተኛ፤ አዛውንቶችን እና ወላጆችን አክባሪ፤ ለሀገሩ ታማኝ፤ የጀግንነት መፍለቂያ፤ የሰላም ተምሳሌት ነው የአማራ ሕዝብ።
ይህ ሕዝብ በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደር፤ ሌሎች የብሔር ወንድሞቹን አቅፎ የያዘ፤ ለጋራ ዕድገት በጋራ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚቆም ነው።
አብሮነት፣ አካታችነት፣ ስለ ሀገር መዋደቅ እና ከወንድሞቹ ጋር በእኩልነት መጓዝ በፍቅር መኖርን ያውቅበታል።
የስብዕና ማማ ባለቤት የኾነው ይህ ሕዝብ ለዘመናት ስለ አብሮነት ተዋድቋል፣ በችግር ወቅት የመነጋገር የመወያየት ባሕሉ ደግሞ በሌሎችም ዘንድ በአርዓያነት የሚጠቀስ ነው።
አልፎ አልፎ የሚፈጠሩ የእርስ በእርስ ግጭቶችን በሽምግልና ሥርዓት በውይይት ይፈታል። ይህም ለዘመናት ሰላሙን እና አንድነቱን ጠብቆ እንዲዘልቅ አድርጎታል። የሰሜኑን ጦርነት ተከትሎ ግን በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ግጭት ዛሬም እንደቀጠለ ነው።
በግጭቱ ምክንያት እናት ይጦረኛል ያለችውን ልጅ አጥታለች። ልጅ እናቱን መቅበር ሳይችል ዐይኗ እንደናፈቀው ሳይመለከታት፣ አፈር ሳያለብሳት ቀርቷል። ነብሰ ጡር እናቶች ሆስፒታል ሳይደርሱ መንገድ ላይ ቀርተዋል። ክልሉ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳቶችን እንዲያስተናግድ አድርጎታል።
በጫካ የሚገኙ ታጣቂዎች የሕዝብን ጥቅም አለማስቀደም፤ እውነተኛ ውይይትን አለመፈለግ ግጭቱ እንዲራዘም ማድረጉን መንግሥት በተለያዬ ጊዜ ያወጣቸው መግለጫዎች ያሳያሉ።
የክልሉ መንግሥት የጫካ ትግልን አማራጭ ላደረጉ ታጣቂዎች በተለያዩ ጊዜያት የሰላም ጥሪን እያስተላለፈ ነው።
ሕዝቡ በዘራፊ እና በወንበዴዎች ጉዳት እየደረሰበት በመኾኑ ሰላሙን ሊያጸና ይገባል ነው ያሉት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ.ር) በዚሁ ወቅት በደብረ ማርቆስ ባደረጉት ንግግር ለምለም ሀገር ይዘን ተግባብተን፣ ተዋደን ሀገርን መሥራት ሲገባን፤ ባንግባባም ተወያይተን፣ ተነጋግረን ሳንጋደል፣ አብረን መኖር ሲገባን፤ ክፉ ክፉውን የምናስብ መልካሙን የምንገፋ መኾን የለብንም ብለዋል።
በጋራ በመታገል ሕገወጦችን በማጥፋት ሰላም እና ልማትን ማረጋገጥ ያስፈልጋልም ነው ያሉት። ችግሮችን በውይይት በመፍታት፤ በትልቅ ጉዳይ ላይ በመሠብሠብ እና በመተባበር የሁሉም ሰው የጋራ መሻት የኾነውን ሰላም እና ልማት በጋራ ለማስፈጸም መጣር ያስፈልጋልም ነው ያሉት።
መንግሥት ከሕዝብ ጋር በመኾን ሊወያዩ ሊነጋገሩ የሚፈልጉ አካላትን ለመቀበል የሰላም በሩ ሁሌም ክፍት ነው ብለዋል።
የማያግባቡ ነገሮችን በሰላማዊ እና በሠለጠነ የፖለቲካ አግባብ መነጋገር ይቻላል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከዛ ውጭ ያለው አማራጭ ኢትዮጵያን አይጠቅምም ነው ያሉት። ግጭት ሊበቃን ይገባል በጋራ መወሰን ያስፈልጋልም ብለዋል።
ከጫካ ትግል ወደ ሰላማዊ ውይይት ለማምራት ከማን ምን ይጠበቃል? እርስዎ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ይላሉ? ሃሳብዎን በሃሳብ መስጫ ሳጥኑ ላይ ያጋሩን
።
#አሚኮ_ዜና#የሰላም_ጥሪ#አማራክልል#ኢትዮጵያ 
#ባሕር_ዳር:ሐምሌ 06/2018 ዓ.ም
በያየህ ፈንቴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
