
የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን (አሚኮ) የነገዋን ሀገር የምንረከብበትን ብቁ ትውልድ ለመቅረጽ በሚደረገው ዘርፈ ብዙ ጥረት ውስጥ የበኩሉን አሻራ እያኖረ ይገኛል። ተቋሙ በትምህርት ዘርፉ ቁሳቁስ ማሟላት ለማይችሉ እና በተለያዩ ምክንያቶች ለተቸገሩ ተማሪዎች እገዛ የሚውል የትምህርት ቁሳቁስ ከተቋሙ የሥራ ኃላፊዎች እና ሠራተኞች የማሠባሠብ መርሐግብር በይፋ አስጀምሯል።
ይህ ንቅናቄ ሚዲያ መረጃ ማድረሻ ብቻ ሳይሆን፣ በተግባር ማኅበረሰብን መገንቢያና የትውልድ ቀራጭ ትልቅ ተቋም መኾኑን በተግባር ያሳየ ነው።
“እኛ በወላጆቻችን እና በአጋዦቻችን እገዛ ተምረን እዚህ ተገናኝተናል፤ ባንማር ኑሮ አብረን እየሠራን ያለን ሰዎች አንገናኝም ነበር” ያሉት ዋና ሥራ አሥፈጻሚው፣ ታዳጊ ወንድም እህቶችን በማገዝ ተተኪ ማፍራት የዜግነት ግዴታ መኾኑን ገልጸዋል። ዓላማውን ለማሳካት የአሚኮ ቤተሰቦችም መረባረብ እንደሚገባቸው አሳስበዋል።
ዛሬ በጎ ልብ በማሳየት የታገዙ ተማሪዎች በቀጣይ በልዩ ልዩ ዘርፎች መልሰው ማኅበረሰቡን ያግዛሉ። ሰው ለህሊናው እርካታ እና ለመንፈሳዊ በረከት ሲል ድጋፍ ለሚፈልጉ የማኅበረሰብ ክፍሎች ከትምህርት ቁሳቁስ ባሻገር የቻለውን ድጋፍ ማድረግ ትውልድ ላይ ኀላፊነትን መወጣት ነው። እርሰዎ በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ሀሳብ አለዎት? በአስተያየት መስጫ ሀሳበዎን ያጋሩን።
#ባሕር ዳር ሐምሌ 02 ቀን 2018 ዓ.ም
