በአማራ ክልል በቀጣይ ቀናት የሚጠበቀውን የአየር ኹኔታ ምን ይመስላል?

3
ባሕር ዳር: ሐምሌ 02/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ወቅቱ አርሶ አደሩ ዘር የሚዘራበት ነው። ለዚህ ሥራ ደግሞ ዝናብ ማግኘት ወሳኙ ነገር ነው። ለመኾኑ በአማራ ክልል በቀጣይ ቀናት የሚጠበቀው የአየር ኹኔታ ምን ይመስላል?
በምዕራብ አማራ የሚቲዮሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል የሚቲዮሮሎጂ ሳይንስ ረዳት ተመራማሪ እንደግ አንለይን ጠይቀናል።
ተመራማሪው እንዳሉት ባለፉት አስር ቀናት በምዕራብ አማራ በአብዛኛው ዞኖች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ተመዝግቧል።
በአዊ ዞን እና አካባቢው ደግሞ እስከ 30 ሚሊ ሜትር እና ከዚያ በላይ የሚደርስ ከባድ ዝናብ መመዝገቡን ገልጸዋል።
በአንጻራዊነት በምሥራቅ አማራ ደረቅ የአየር ኹኔታ የተመዘገበበት ነበር። ነገር ግን ከሰኔ 30 ጀምሮ በሰሜን ሸዋ፣ ኦሮሞ ብሄረሰብ ዞን፣ ደቡብ ወሎ እና በጥቂት ሰሜን ወሎ አካባቢዎች ቀላል መጠን ያለው ዝናብ ተመዝግቧል ነው ያሉት።
🌧 በቀጣይ አስር ቀናት የሚጠበቀው ኹኔታስ?
በቀጣይ አስር ቀናት የዝናብ መጠኑም ይኹን የሥርጭቱ ኹኔታ እየተሻሻለ እንደሚሄድ ይጠበቃል አሉ ተመራማሪው።
በምዕራብ አማራም ኾነ በምሥራቅ አማራ ዞኖች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ይጠበቃል ነው ያሉት።
በተለይም በምዕራብ አማራ (አዊ ዞን፣ ምሥራቅ እና ምዕራብ ጎጃም፣ እንዲኹም ማዕከላዊ ጎንደር) ደግሞ ከ30 ሚሊ ሜትር በላይ የኾነ ዝናብ ሊኖር እንደሚችል ኹኔታዎች ይጠቁማሉ ብለዋል።
⚠️ ሊወሰዱ የሚገባቸው የጥንቃቄዎች፦
👉. አርሶ አደሩ ያለውን እርጥበት በአግባቡ መጠቀም እና ፈጥነው ሊደርሱ የሚችሉ የሰብል ዝርያዎችን መዝራት
👉. ከከፍተኛ ሙቀት እና ከእርጥበት መለዋወጥ ጋር ተያይዞ የሰብል ተባዮች ሊከሰቱ ስለሚችሉ ተገቢው ክትትል ማድረግ
👉. በተራራማ እና ለጎርፍ ተጋላጭ በኾኑ የምዕራብ አማራ አካባቢዎች የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የጎርፍ አደጋን ለመከላከል አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግን የሚቲዮሮሎጂ ሳይንስ ረዳት ተመራማሪው እንደግ አንለይ መክረዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous article“ዛሬ በጎ ልብ በማሳየት ያገዝናቸው ታዳጊዎች በቀጣይ የማኅበረሰቡ አጋዥ ናቸው” ዋና ሥራ አሥፈጻሚ ሙሉቀን ሰጥዬ