
“አረንጓዴ ዐሻራ ከእሳቤ እስከ ትግበራው ኢትዮጵያ የተገለጠችበት ደማቅ ብሔራዊ ቀለም ነው።” ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማህበራዊ ገጻቸው መልእክት አስተላልፈዋል፦
በእሳቤዎች የተመሩ የታላላቅ ስልጣኔዎች እና የነጠሩ እውቀቶች ማሕደር በሆነችው ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ እሳቤ ይህ ትውልድ የአርቆ አሳቢ አባቶቹ ልጅ መሆኑን ያስመሰከረበት የጠራ ሐቅ ነው።
የአየር ንብረት ለውጥ በተለምዶ ከምናየው ተደጋጋሚ የኮንፍረንስ እቅድ በተሻገረ፣ አፈር ነክቶ ጭቃ ረግጦ በትጋት በመስራት የሚመጣ የትጋት ውጤት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ ከማመንጨት እስከ ትግበራ በመምራትና በመሥራት ግንባር ቀደም ሆነው አሳይተውናል።
የጠራ እቅድ እና መዳረሻ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ ሀገራዊ ፕሮጀክት ከታዳጊ ህጻናት ጀምሮ የእድሜ በረከት እስከበዛላቸው አረጋውያን የተሳተፉበት ታሪካዊ የልማት ዘመቻ ሆኗል።
የኢትዮጵያ ልጆች ለዓመታት በስኬት የተገበሩት ይህ ኢኒሼቲቭ ሀገራችንን በዓለም ፊት በክብር እያስጠራ ያለ የለውጥ ምልክት እስከመሆን ደርሷል።
እንደ ኮፕ 32 ያሉ ዓለም አቀፍ መድረኮችን የማስተናገድ እድሎችም በተባበረ ክንድ በተደመረ እሳቤ የመስራታችን ውጤቶች እና የብሔራዊ ዐሻራችን ሽልማቶች ናቸው።
በአረንጓዴ ዐሻራምና በሌሎች የለውጥ ግቦቻችን የታዩ የትጋት ድል ፍሬዎች በተደመሩ ጥረቶች ኢትዮጵያ በእርግጥም እየለማች እየፈካች ትገኛለች። በሁሉም መስክ አቅደን የምንተገብራቸው ህልሞቻችን እስኪሳኩ ድረስ በብርታት እንሠራለን።
ተስፋን እንትከል!
#አሚኮ #ኢትዮጵያ #አረንጓዴ_አሻራ
