
እንጅባራ፡ ግንቦት 24/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ዛሬ እየተካሄደ በሚገኘው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በእንጅባራ ከተማ የኮሶበር ምርጫ ክልል መራጮች ያለምንም ግፊት “ይበጀናል” የሚሉትን ፓርቲ በነጻነት እየመረጡ መኾናቸውን ገልጸዋል።
የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች በሕጉ መሠረት በማለዳው 12 ሰዓት ላይ በታዛቢዎች እና በፓርቲ ወኪሎች ፊት ቁሳቁሶችን በመክፈት ሂደቱን በሰዓቱ አስጀምረዋል። መራጮችም የሀገሪቱን የዴሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት በማለዳው ተገኝተው ድምጽ መስጠታቸውን ተናግረዋል።
በዕለቱ ለነፍሰ ጡሮች፣ ለአረጋውያን እና ለአካል ጉዳተኞች ቅድሚያ ተሰጥቶ ሳይንገላቱ እንዲመርጡ መደረጉን እና አጠቃላይ የድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ ምስጢራዊነቱን ጠብቆ በሰላማዊ መንገድ እየተከናወነ መኾኑን ገለልተኛ ታዛቢዎች አረጋግጠዋል።
የጣቢያው አስፈጻሚዎች የተሰጣቸውን ኀላፊነት ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት እያከናወኑ መኾኑን ጠቁመዋል። የጸጥታ ኃይሉም ለምርጫው ሰላማዊነት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
ዘጋቢ፦ በቃሉ ፈረደ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
