
ጎንደር: ግንቦት 13/2018 ዓ .ም ( አሚኮ) የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን በጎንደር ከተማ ጠዳ የሥልጠና ማዕከል የሰላምን አማራጭ ለተቀበሉ የቀድሞ ታጣቂዎች የተሃድሶ ሥልጠና መሥጠት ጀምሯል ።
በመርሃ ግብሩ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ ጨምሮ ከፍተኛ የፌደራል እና የክልል የሥራ ኃላፊዎች ፣ የጦር መኮንኖች ፣ የሰላምን አማራጭ ቀደም ብለው የተቀበሉና በቅርብ የገቡ የቀድሞ ታጣቂዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
መርሀ ግብሩን በንግግር የከፈቱት የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን ኮሚሽነር ተመስገን ጥላሁን ሰላምን መርጠው ለመጡ የቀድሞ ታጣቂዎች ምስጋና አቅርበዋል።
ወጣቶች ከሥልጠናው በኋላ ንቁ ማኅበራዊ ተሳታፊ እንዲሆኑም ጠይቀዋል።
እንደ ኮሚሽነሩ ገለጻ እስካሁን በሀገሪቱ ታጥቀው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ከ88 ሽህ በላይ የቀድሞ ታጣቂዎች ሥልጠና የመሥጠትና መልሶ የማቋቋም ተግባር መከናወኑን ጠቅሰዋል።
አሁንም በተጥቅ ትግል ያሉ ወጣቶች የሰላም አማራጭ እንዲቀበሉ ጠይቀዋል።
የአማራ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ኀላፊ በሪሁን መንግስቱ በበኩላቸው ሰላም በመወያየትና በመደማመጥ ማረጋገጥ እንደሚገባ ጠቅሰዋል።
ውይይቱም በጋራ መሥራትን ፣ መተጋገዝን እና አብሮነትን ለማስገንዘብ መኾኑን አስገንዝበዋል።
የሰላም ጉዞ በአንድ አካል ብቻ የሚስተካከል ባለመሆኑ በጋራ ልንስራ ይገባልም ነው ያሉት።
መገዳደል ሊቆም እንደሚገባ መልዕክት ያስተላለፉት ደግሞ የጎንደር አካባቢ መከላከያ አዛዥ ብርጋዴል ጀኔራል መለስ በለጠ ናቸው።
ለዘላቂ ሰላም በጋራ ለመስራት ዝግጁ መኾናቸውንም ተናግረዋል።
በአማራ ክልል ከ30 ሽህ በላይ የቀድሞ ታጣቂዎች የሰላም አማራጭ ተቀብለዋል ያሉት በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአሥስተዳደር ጉዳዮች ዘርፍ አሥተባባሪ አማኑኤል ፈረደ(ዶ/ር) እስካሁን ከ15 ሽህ በላዩ ሥልጠና መውሰዳቸውን ገልጸዋል።
ችግሮችን በነፍጥ ሳይሆን በንግግር እና ውይይት መፍታት ባሕል ማድረግ እንደሚገባም አንስተዋል።
ተደራጅተው ወደ ስራ መግባት ለሚፈልጉ ወጣቶች በክህሎታቸው ሥራ እንዲጀምሩ ተደርጓል ያሉት አስተባባሪዉ ቀሪዎችንም ወደሥራ ለማስገባት እየተሰራ ነው ብለዋል።
በሥልጠናው ያነጋገርናቸው ወጣቶች በበኩላቸው ሰላም የሁለም ነገር መሰረት በመኾኑ ለዘላቂ ሰላም በትኩረት እንደሚሰሩ ነግረውናል።
ከሥልጠናው በኋላ በማኅበራዊ አገልግሎቶች ለመሳተፍ ቁርጠኛ መኾናቸውንም አንስተዋል።
በትጥቅ ትግል የሚንቀሳቀሱ ወጣቶች የሰላም አማራጭ እንዲቀበሉ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ተናግረዋል።
ዘጋቢ:- አዲስ አለማየሁ
