የምርጫ ቅስቀሳ የሕዝብን ደኅንነት ያስቀደመ የሀሳብ መድረክ ይሁን!

7
🗳️📢ባሕር ዳር: ግንቦት 11/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬታማ እንዲኾን ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ትልቅ ኀላፊነት አለባቸው፡፡ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ፓርቲዎቹ በሚያደርጓቸው ሕዝባዊ ሥብሠባዎች እና የዓደባባይ ንግግሮች የጥላቻ እና ስሜት ቀስቃሽ ቃላትን ማስወገድ ይጠበቅባቸዋል፡፡
በሀሳብ የበላይነት ብቻ በማመን በቅስቀሳ ወቅት ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ በአማራ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገልጸዋል፡፡
በአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባሕል ግንባታ ዘርፍ ኀላፊ መስፍን አበጀ (ዶ.ር) ፓርቲዎች በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት የሚያስተላልፉት መልዕክት ለብጥብጥ እና ለሁከት የሚዳርግ እንዳይኾን በጥንቃቄ ሊመራ ይገባል ብለዋል፡፡
🤝 የሕዝብን አንድነት እና ሰላምን ያስቀደመ ቅስቀሳ ማድረግ በፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትም አቋም የተወሰደበት መኾኑንም ጠቁመዋል። ደጋፊዎቻቸው በስሜት ተገፋፍተው ወደ ግጭት እንዳይገቡ ፓርቲዎቹ በኀላፊነት መንቀሳቀስ እንደሚገባቸው ነው የገለጹት፡፡
ብልጽግና ፓርቲም ይህንኑ መመሪያ መሠረት አድርጎ በምረጡኝ ቅስቀሳዎቹ ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኀይል ንቅናቄ (አዴኃን) ሊቀ መንበር ተስፋሁን ዓለምነህ ስኬታማ ምርጫ የሚካሄደው በምርጫ ቦርድ የተቀመጡ ሕጎችን እና ደንቦችን በአግባቡ አክብሮ መንቀሳቀስ ሲቻል ነው ብለዋል፡፡
መብትን ለመጠቀም ግዴታን በአግባቡ መወጣት እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ በቅስቀሳ ወቅት አንዱ የሌላውን ስም በማያጎድፍ መልኩ መንቀሳቀስ የሠለጠነ ፖለቲካ መገለጫ መኾኑንም አንስተዋል።
⚖️ በሂደቱ የሚያጋጥሙ ችግሮች ቢኖሩ እንኳ በምርጫ ቦርድ ሕግ መሠረት እየፈቱ የመጨረሻ ዳኝነቱን ለሕዝቡ መስጠት እና የሕዝቡን ውሳኔ መቀበል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
አዴኃንም ይህንን መሠረት በማድረግ የሕዝብን ሰላም እና ደኅንነት ባስቀደመ መልኩ ለምርጫው እየተዘጋጀ መኾኑን ጠቁመዋል።
ዘጋቢ:- አሰፋ ልጥገበው
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

S
Previous articleበምዕራብ ጎንደር ዞን ለምርጫው የቅድመ ዝግጅት ሥራ ተጠናቅቋል።
Next articleሥልጣን የሚገኘው በካርድ ብቻ ነው።