
ባሕር ዳር: ግንቦት 10/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ለልማት እና ለዜጎች እድገት ይበጃል የሚሉትን ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን በጻግብጂ ወረዳ የአርሸርዋ ከተማ ነዋሪዎች ገልጸዋል።
ከአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋር ቆይታ ያደረጉት አቶ ሲሳይ አማረ እና አድማስ ቀነነው በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ላይ በንቃት ለመሳተፍ የምርጫ ካርድ ወስደናል ብለዋል። የድምጽ መስጫውን ቀን በከፍተኛ ጉጉት እየጠበቁ መኾናቸውንም ገልጸዋል፡፡
ሀገርን የሚያሻግር፤ ለልማት እና ለዜጎች እድገት ይበጃል የሚሉትን ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ነው የተናገሩት። ምርጫው ተዓማኒ፣ ፍትሐዊ እና ዴሞክራሲያዊ ኾኖ እንዲከናወን የዜግነት ግዴታቸውን እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።
የምርጫ ሂደቱ በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ እንደኾነ መታዘባቸውንም አንስተዋል። ፓርቲዎች አማራጭ ሀሳባቸውን ለማቅረብ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴም አድንቀዋል።
በኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የጊዜ ሰሌዳ መሠረት የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የድምጽ መስጫ ዕለት ግንቦት 24/2018 ዓ.ም መኾኑ ይታወቃል።
ዘጋቢ፦ ሙላት ክንፉ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
