
ባሕር ዳር: ግንቦት 09/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የጣና ክፍለ ከተማ አባላት እና ደጋፊዎች በተገኙበት የአደባባይ ላይ የምርጫ ቅስቀሳ አካሂዷል።
የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ሞላ ሁሴን የባሕር ዳር ነዋሪዎች ለሰላም፣ ለልማት፣ ለእድገት እና ለብልጽግና ቁልፍ ሚና እየተጫወቱ መኾናቸውን አረጋግጠዋል።
በመድረኩ የተገኙት የሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኀላፊ አማረ ዓለሙ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የተጀመረውን ሁለንተናዊ ብልጽግና እና የልማት ሥራዎችን ለማስቀጠል ከሕዝብ ጋር የቀጣይ አምስት ዓመታት የሥራ ውል የሚፈረምበት ነው ብለዋል። የአሁኑ ምርጫ በሪፎርሞች ሰፊ ውጤት በተገኘበት ወቅት የሚካሄድ በመኾኑ ሕዝቡ ይህንን መልካም አጋጣሚ ሊጠቀምበት እንደሚገባ ገልጸዋል።
ብልጽግና በተግባር ሠርቶ የሚያሳይ ፓርቲ መኾኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይ አምስት ዓመታት የኮሪደር ልማትን፣ የአረንጓዴ አሻራን፣ ዲጂታላይዜሽንን እና ዘመናዊነትን ለማስፋፋት የታቀዱ ሥራዎችን ለማስቀጠል ሕዝቡ ለፓርቲው ድምጹን እንዲሰጥ ጠይቀዋል።
የአማራ ክልል ማዕድን ቢሮ ኀላፊ ኀይሌ አበበ ብልጽግና ፈተናዎችን ተቋቁሞ ልማትን እያረጋገጠ ያለ የትውልድ ፓርቲ ነው ብለዋል።
ባለፉት አምስት ዓመታት በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በቱሪዝም፣ በማዕድን እና በአካባቢ ልማት ዘርፎች በርካታ ስኬታማ ሥራዎች መከናወናቸውንም ጠቁመዋል።
ዘጋቢ:- ስማቸው አጥናፍ
#አሚኮ #ምርጫ_2018 #ኢትዮጵያ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
https://linktr.ee/Amharamediacorporations
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
