በምርጫ ወቅት ሕግ መጣስ እስከምን ድረስ ያስቀጣል?

5
ባሕር ዳር፡ ግንቦት 06/2018ዓ.ም (አሚኮ) የአንዲት ሀገር የዴሞክራሲ ጉዞ ስኬት የሚለካው የምርጫ ሂደት በጠንካራ የሕግ ማዕቀፍ ሲጠበቅ እና ሕዝብ በነፃነት ድምጹን መስጠት ሲችል ነው።
ምርጫ የዜጎች የሥልጣን ባለቤትነት መገለጫ ነው። ይህ መብት ያለ አግባብ እንዳይቀለበስ የራሱ የኾኑ የሕግ ድንጋጌዎች አሉት። ብዙዎቻችን መምረጥ እና መመረጥን እንደ መብት ብቻ እናየዋለን፤ ነገር ግን በዚህ ሂደት ውስጥ የሚፈጸሙ ጥፋቶች ከእስራት እስከ መብት መታገድ የሚያደርሱ ከባድ ቅጣቶችን እንደሚያስከትሉ ያውቃሉ?
👉የሕግ ባለሙያው ዕይታ የአማራ ክልል የፍትሕ ቢሮ የመደበኛ ወንጀሎች አቃቢ ሕግ ባለሙያ ንጉሥ አንዳርጌ እንደሚሉት መንግሥታዊ የሥልጣን ባለቤት መኾን የሚቻለው በምርጫና በምርጫ ብቻ ነው።
ይህ መሠረታዊ መርሕ በኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 9(3) ላይ በግልጽ ተደንግጓል ይላሉ።
ምርጫው ሰላማዊ እና ፍትሐዊ እንዲኾን ከቅድመ ምርጫ እስከ ድምጽ ቆጠራ ድረስ ሊከበሩ የሚገባቸው የሕግ ማዕቀፎች መኖራቸውን ጠቁመዋል።
👉በምርጫ ወቅት የተከለከሉ ዋና ዋና ተግባራት
ሕጉ ማንኛውም ዜጋ፣ ዕጩ ተመራጭ ወይም የፖለቲካ ፓርቲ እንዳይፈጽማቸው በጥብቅ የከለከላቸው ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው።
👉የዜጎችን መብት ማወክ፦
ለምርጫ ተብሎ ሥብሠባ በማድረግ ሂደቱን መረበሽ ወይም ዜጎች እንዳይመርጡ እና እንዳይመረጡ እንቅፋት መኾን።
👉የዕድሜ ማጭበርበር፦
ዕድሜያቸው ያልደረሰ ሕፃናት እንዲመዘገቡ ወይም እንዲመርጡ ማግባባት እና መገፋፋት።
👉ሙስና እና ጉቦ፦
የምርጫ ውጤትን ለማዛባት የእጅ መንሻ (ጉቦ) መስጠት ወይም መቀበል።
👉የሰነድ እና የቁሳቁስ ጥቃት፦
የምርጫ ሳጥን እና ኮሮጆዎችን መስረቅ ወይም ማጥፋት፣ የድምጽ መስጫ ወረቀቶችን ማበላሸት እና የምርጫ ፖስተሮችን ኾን ብሎ መቅደድ። የምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ ከተከለከለ በኋላ ማንኛውንም ዓይነት የቅስቀሳ ሥራ ማከናወን።
👉የሀብትና የሰው ኀይል ማጭበርበር፦
ለምዝገባ የሚቀርቡ አባላትን ቁጥር ማጭበርበር፣ ሀሰተኛ የሀብት እና የዕዳ መግለጫ ማቅረብ፣ በመንግሥት እና በሕዝብ የተመደበን የምርጫ በጀት ለሌላ ዓላማ ማዋል፣ በምርጫ ወቅት የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ በፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ (1162/2011) በጥብቅ የተከለከሉ ናቸው።
👉ቅጣት እና ተጠያቂነት ሕግን መጣስ የሚያስከትለው ውጤት የገንዘብ መቀጮ ብቻ አይደለም። እንደ ባለሙያው ንጉሥ ገለጻ በአዋጅ ቁጥር 881/2007 መሠረት የወንጀል ተጠያቂነትን የሚያስከትል ነው። ጥፋተኛ ኾኖ የተገኘ አካል ከገንዘብ እና ከእስራት ቅጣት ባሻገር የመምረጥ እና የመመረጥ መብቱ እንደሚታገድም ነው የገለጹት።
ምርጫ የነገ ዕጣ ፈንታችንን የምንወስንበት ታላቅ መድረክ ነው። ይህ መድረክ በሕገ-ወጥነት እንዳይበላሽ ደግሞ በሕገ መንግሥቱ የተደነገጉ የምርጫ ሕጎችን እና አዋጆችን ማክበር እና ተገዥ መኾን ግድ ይላል። ሕግን ማክበር መብትን ማክበር ነውና።
ዘጋቢ ፦ ቴዎድሮስ ደሴ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !
Previous articleምርጫ ለሀገር!
Next articleሀገር በዴሞክራሲያዊ ምርጫ እንድትመራ የመምህራን ሚና ትልቅ ነው።