
የአማራ ክልል ምክር ቤት ከተዋረድ የምክር ቤት አባላት ጋር ሲያካሂድ የቆየውን የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 ዕቅድ ትውውቅ መድረክ አጠናቋል።
የምክር ቤቱ ምክትል አፈጉባኤ አማረ ሰጤ ለሦሥት ቀናት በቆየው መድረክ ከተዋረድ የምክር ቤት አባላት ጋር በ 2018 በጀት ዓመት የነበረውን አፈጻጸም እና የ2019 ዕቅድ ትውውቅ መካሄዱን ገልጸዋል። በመድረኩ የተዋረድ ምክር ቤት አባላት ጠንካራ እና ደካማ ጎኖች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
የምክር ቤቱ የሥራ አፈጻጸም ጠንካራ እና ደካማ ጎን ለገለልተኛ አካል መቅረቡን ጠቅሰው አጠቃላይ አፈጻጸሙ ሲታይ ውጤታማ መኾኑን ገልጸዋል።
7ኛ ዙር የተመረጠው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤቶች የታዩት ክፍተቶችን ማረም እንዳለባቸው አጽንኦት መሰጠቱን ምክትል አፈጉባኤው አንስተዋል።
አስተማማኝ ሰላም ባለባቸው አካባቢዎች ክትትል እና ድጋፉን በማጠናከር ምክር ቤቶች አውራ ተቆማት እንዲኾኑ መግባባት ተፈጥሯልም ነው ያሉት።
የምክር ቤቶች መዋቅር በአባላቱ ይነሳ የነበረ አንዱ ጉዳይ ነው ያሉት አቶ አማረ በክልሉ መንግሥት ምላሽ በማግኘቱ በአባላቱ ዘንድ ደስታን ፈጥሯል ብለዋል። ይህም አባላቱ በተሻለ መንገድ ኀላፊነታቸውን እንዲወጡ መነሳሳት ፈጥሮላቸዋል ነው ያሉት።
ሌላው ያነሱት ጉዳይ የተዋረድ ምክር ቤት አባላት ምርጫ ጉዳይ ሲኾን ለ14 ዓመታት ሳይካሄድ በመቆየቱ በክልል ምክር ቤቱ ሥራ ላይ እንቅፋት ፈጥሯል ብለዋል።
በጉዳዩ ላይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ምርጫ ቦርድ እና የክልል ምክር ቤት ባሉበት ውይይት መደረጉንም ጠቁመዋል።
ምርጫውን ዘንድሮ እናካሂዳለን የሚል ስምምነት መፈጠሩን ጠቁመው ነገር ግን በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሚመራ ነው ብለዋል። በዚህ ዓመት ይደረጋል የሚል ዕምነት እንዳላቸውም ነው የተናገሩት።
መድረኩ በ2018 በጀት ዓመት የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የተዋረድ ምክር ቤቶች ዕውቅና እና ሽልማት በመስጠት ተጠናቋል።
ዘጋቢ፦ አድኖ ማርቆስ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
