
”ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025″ ስትራቴጂ ያስመዘገባቸውን ስኬቶች መሠረት በማድረግ የተነደፈው “ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030” ፣ ሀገሪቱ በቴክኖሎጂ ታጅባ ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገት እንድታስመዘግብ የሚያስችል የትውልድ ርዕይ ማዕቀፍ ነው።
ይህ ስትራቴጂ የዲጂታል አገልግሎቶችን ተደራሽነት ከማስፋት ባለፈ የተቋማትን አሠራር በማዘመን ዜጎች በዓለም አቀፍ የዲጂታል መስመር ተወዳዳሪ እንዲኾኑ ለማስቻል ትልልቅ ዓላማዎችን አንግቦ እየተተገበረ ይገኛል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የ«ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030» ስትራቴጂ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ላይ እንደገለጹት፣ ባለፉት አምስት ዓመታት ተግባራዊ የተደረገው «ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025» ስትራቴጂ ስኬታማ ኾኖ መጠናቀቁን አውስተዋል።
አዲሱ የ«ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030» ስትራቴጂ ሦሥት ቁልፍ ዓላማዎች እንዳሉት የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የመጀመሪያው ሁሉም ዜጎች ባሉበት ቦታ ኾነው የሚፈልጉትን አገልግሎት የሚያገኙበትን ዕድል መፍጠር እንደኾነ ገልጸዋል።
ሁለተኛው ዜጎችን እኩል የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ ሲኾን፣ ሦሥተኛው ደግሞ በዜጎች እና በተቋማት መካከል ጠንካራ መተማመንን መገንባት እንደኾነ አስረድተዋል።
በሂደቱም በመንግሥት እና በግል ተቋማት መካከል የተቀናጀ ግንኙነት የመፍጠር፣ አስተማማኝ የሳይበር ጥቃት መከላከል ሥርዓት የመዘርጋት እና ቴክኖሎጂ-ሳቢ ትውልድ የመገንባት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
አክለውም የሳይበር ደኅንነትን ማረጋገጥ እና የዜጎችን የዲጂታል አጠቃቀም ማሳደግ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ያሰመሩበት ሲኾን በቴክኖሎጂ የበለፀገ ትውልድ ሲፈጠር የሀገርን ባሕል፣ ፍላጎት እና ጥቅም ባልነካ መልኩ መኾን እንዳለበት አስገንዝበዋል።
የዲጂታል ሉዓላዊነት የዘመኑ ወሳኝ ጉዳይ በመኾኑ ኢትዮጵያ በዚህ ዘርፍ ራሷን መቻል እንዳለባት እና ለዚህም የዘርፉን ተቋማት አቅም የማጎልበት ሥራ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል።
የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ.ር) የሰው ልጅ ዕውቀት እና የአኗኗር ዘይቤ በከፍተኛ ፍጥነት እየተለወጠ መምጣቱን በማንሳት በዲጂታል የጎለበተ ማኅበረሰብ ለመፍጠር እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል።
ባለፉት ዓመታት የተቀረጹ ፖሊሲዎች እና ስትራቴጂዎች አጠቃላይ የዲጂታል ኢኮኖሚውን ለመገንባት ሰፊ መሠረት መጣላቸውን ያመለከቱት ሚኒስትሩ ጠንካራ ተቋማትን በመገንባት «ነገ ሀገራችን ምን ትኾናለች?» የሚለውን ታሳቢ ያደረገ አቅጣጫ መያዙን ገልጸዋል።
ባለፉት ዓመታት የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ቀልጣፋ አሠራር መዘርጋቱን የጠቆሙት ሚኒስትሩ በቀጣይም የነገ ልጆች የሚረከቧትን ሀገር በቴክኖሎጂ ከፍ ወዳለ ደረጃ ማሸጋገር እንደሚገባ አሳስበዋል።
ለዚህም ተቋማቸው ከሃሳብ ማመንጨት ጀምሮ እስከ ግዙፍ የዲጂታል ማዕቀፎች ዝግጅት ድረስ በትጋት እየሠራ ይገኛል።
በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (ኤአይ) እና በኮዲንግ ኢኒሼቲቮች የታገዙ የዲጂታል ክህሎት እና የፈጠራ ሥራዎችም ወጣቶችን ለነገው ዓለም ዝግጁ ለማድረግ ታቅደዋል።
በአጠቃላይ «ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030» ከቀላል የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ባሻገር በፈጠራ እና በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ዲጂታል ኢኮኖሚ በመገንባት የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ እውን የሚያደርግ ታላቅ ሀገራዊ ምዕራፍ ነው።
በሥራውድንቅ ደሳለው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
