“2019 ዓ.ም በአንድነት ቆመን ለወደፊቷ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሠረት የምንጥልበት ዓመት ነው” ርእሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ

5
በሀረሪ ክልል የጳጉሜን 5 “የነገ ቀን” መርሐ-ግብር የክልሉ ርእሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ፣ የክልሉ ከፍተኛ መሪዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከብሯል።
ርእሰ መሥተዳድሩ በመርሐ-ግብሩ ላይ ባስተላለፉት የዘመን መለወጫ መልዕክት፣ የአዲስ ዓመት መባቻ ያለፈውን ገምግመን፣ አዲሱን ዓመት በላቀ የተስፋ እና የሥራ መንፈስ የምንቀበልበት አጋጣሚ መኾኑን ገልጸዋል።
👉የ2018 ዓ.ም ዋና ዋና ስኬቶች፦
የተጠናቀቀው የ2018 ዓ.ም በሁሉም ዘርፎች አበረታች ውጤቶች የተመዘገቡበት ልዩ እና ታሪካዊ ዓመት እንደነበር ርእሰ መሥተዳድር ኦርዲን ጠቅሰው የሚከተሉትን ዋና ዋና አበይት ኩነቶች አጉልተዋል፦
👉ፖለቲካዊና ዲሞክራሲያዊ ምዕራፍ፦ 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ የተካሄደበት እንዲሁም በሀገራዊ ምክክሩ ለዘመናት የቆዩ መሠረታዊ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ለብሔራዊ መግባባት እና ለዘላቂ ሰላም መሠረት የተጣለበት ዓመት ነበር።
👉የማኅበራዊ እና ኢኮኖሚ ልማት፦ የዜጎችን ሕይወት የሚያሻሽሉ ታላላቅ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። የከተሞችን ገጽታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማቶች፣ የቱሪዝም መስህቦች እና ሰው-ተኮር ፕሮጀክቶች በፍጥነት እየተገነቡ ይገኛሉ።
👉የምግብ ዋስትና እና አካባቢ ጥበቃ፦ በአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር በተከናወኑ ተግባራት የግብርና እና የአካባቢ ልማት ሥራዎችን በማጎልበት ምርታማነት አድጓል፤ የምግብ ዋስትናም እየተረጋገጠ ይገኛል።
👉ክልላዊ ውህደት እና የሥራ ባሕል፦ በክልሉ ጠንካራ የአመራር ውህደት የተፈጠረበት፣ ሌት ተቀን የመሥራት ባሕል የሰረጸበት፣ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የተፈጠረበት እና በኮሪደር ልማት አስደናቂ እመርታ የተመዘገበበት ስኬታማ ዓመት ነበር።
👉የታሪክ ትስስር እና የ2019 ዓ.ም አቅጣጫ ቀደም ሲል ሀገርን “ወዳጅ እና ጠላት” በሚሉ አብዮታዊ አስተሳሰቦች በመከፋፈል የሺህ ዓመታት የታሪክ ትስስራችን ወደ መጠላላት ተቀይሮ ጊዜያችን፣ ጉልበታችን እና ዕውቀታችን በመገፋፋት ላይ እንዲባክን መደረጉን ርእሰ መሥተዳድሩ አስታውሰዋል።
ዛሬ ግን ያ የጨለማ ዘመን አብቅቶ የፍቅር፣ የአብሮነት እና የመከባበር ባሕላችን እየተመለሰ፣ እንደ ነውር ይታይ የነበረው ወንድማማችነት እና የጋራ ማንነታችን እያበበ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም የቋንቋ፣ የባሕል እና የታሪክ ብዝኀነት ለኅብረ-ብሔራዊ አንድነታችን እና ለጋራ ብሔራዊ ትርክታችን ውበት መኾናቸውን አብራርተዋል።
አክለውም የፀረ-ሰላም ኀይሎችን እኩይ እንቅስቃሴ በማክሸፍ፣ ተቋማትን በማጠናከር እና የሕዝብን ጥያቄዎች በትክክል በመመለስ ላይ እንደሚገኙም ገልጸዋል።
“2019 ዓ.ም ሀገራዊ አንድነታችንን ይበልጥ የምናጠናክርበት፣ የሕግ የበላይነትን የምናረጋግጥበት እና ለወደፊቷ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሠረት የምንጥልበት ዓመት ይኾናል” ያሉት አቶ ኦርዲን በመሪዎች እና በሕዝቡ መካከል የተፈጠረውን የአንድነት እና የመነሳሳት ማዕበል አጠናክሮ ለማስቀጠል ከፍተኛ አደራ ያለ በመኾኑ “ለአፍታም የምንተኛው እንቅልፍ አይኖርም” ሲሉ መልዕክታቸውን አጠናቀዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous articleለነገው ቀን የዲጅታል ትራንስፎርሜሽን እቅዶችን በላቀ ደረጃ በማከናወን የሕዝብን ኑሮ ለማሻሻል ቃል የምንገባበት ዕለት ነው።
Next articleበጋራ ልማት እጅ ለእጅ ተያይዘን ወደ ነገ እንሻገራለን።