በቴክኖሎጂ የተቃኘው የኢትዮጵያ የማንሰራራት ጉዞ!

9
ዛሬ ላይ ቴክኖሎጂ የቅንጦት ጉዳይ አይደለም። የሀገራት ብሔራዊ ደኅንነት፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት እና የጂኦ-ፖለቲካዊ ተጽዕኖ መለኪያ ወደ መኾን ተሸጋግሯል። ኢትዮጵያም ይህንን በመረዳት ጉዞዋን ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ አድርጋለች።
የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ.ር) ኢትዮጵያ የሰው ሠራሽ አስተውሎትን አቅም በተግባር እያረጋገጠች እና ለአፍሪካ ኢኖቬሽን መንገድ እየጠረገች ትገኛለች ብለዋል።
ሀገሪቱ አሁን ለደረሰችበት የቴክኖሎጂ ጉዞ ግን መንገዱ አልጋ በአልጋ አልነበረም። ከጥቂት ዓመታት በፊት ሀገሪቱ በዘርፉ በርካታ መዋቅራዊ ማነቆዎች ነበሩባት። የቴሌኮም ዘርፉ በአንድ የመንግሥት ተቋም ስር ብቻ በመቆየቱ የኢንተርኔት ተደራሽነት እና ጥራት እጅግ ዝቅተኛ ነበረ።
የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩም የፋይናንስ ዘርፉ በወረቀት ላይ የተመሠረተ ኾኖ ቆይቷል። ለፈጠራ ሥራዎች የሚኾን ምቹ ሥነ-ምህዳር እና የላቁ ቴክኖሎጂዎችን የሚመሩ ተቋማት አለመኖራቸውም ሀገሪቱን ከዓለም አቀፉ የዲጂታል አብዮት አግልሏት ቆይቷል።
በቅርብ ጊዜ የተወሰዱ የሪፎርም ርምጃዎች ግን ይህንን የዝግመት አዙሪት ሰብረው ተጨባጭ ውጤቶችን እያሳዩ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የሳይንስ ሙዚየምን ሲመርቁ፣ “ትላንት ሌሎች የፈጠሩትን ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ብቻ ነበርን፤ ዛሬ ግን የራሳችንን አቅም ገንብተን የነገዋን ታላቅ ኢትዮጵያ በራሳችን ልጆች እጅ እንቀርጻለን” ብለዋል።
📱 የቴሌኮም ዘርፉን ሊበራላይዝ በማድረግ የኢንተርኔት ተደራሽነትን በፍጥነት ማሳደግም ተችሏል። በአጭር ጊዜ ውስጥ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተጠቃሚዎችን ያፈራው ቴሌብርም የፋይናንስ አካታችነትን ወደ ላቀ ደረጃ አሸጋግሮታል።
💻 የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፣ የሳይንስ ሙዚየም፣ የአይሲቲ ፓርክ ማስፋፊያ፣ የ5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ሀገሪቱ በቴክኖሎጂ የተካነ የሰው ኀይል ለመፍጠር ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳዩ ናቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩት እና አዲስ የኤ.አይ ዩኒቨርሲቲ ማቋቋምን ጨምሮ በግዙፍ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ጅማሮዎች አማካኝነት ወጣቶቿን ለወደፊቱ በማዘጋጀት ኢትዮጵያ በአፍሪካ ግንባር ቀደም ኾናለች” በማለት የሀገሪቱን ራዕይ መስክረዋል።
⚛️ የነገዋ ኢትዮጵያ ራዕይም ቴክኖሎጂን ከኢኮኖሚ ሞተርነት አልፎ የኅብረተሰቡን የዕለት ተዕለት ኑሮ ወደሚያቀል የልዕልና ደረጃ ማሸጋገር ነው። በሰባቱ የጉባ ብስራቶች ውስጥ የተካተተው የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ማበልጸጊያ ፕሮጀክትም ሀገሪቱ ከአፍሪካ አልፋ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ትልቅ የቴክኖሎጂ ምኞት ያሳያል።
🏙️ ስማርት ከተሞች፣ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ)፣ በሰው ሠራሽ አስተውሎት እና በድሮን የሚታገዝ ዘመናዊ ግብርና፣ ጠንካራ የሳይበር ደኅንነት እና የዳታ ማዕከላት ግንባታ የነገዋ ኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ማረጋገጫዎች ናቸው። በተጨማሪም የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞው ኢትዮጵያ ነገ የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ፈጠራ፣ የኢንቨስትመንት እና የዲጂታል ኢኮኖሚ ማዕከል የሚያደርጉ ናቸው።
✍️ ዘጋቢ፦ ስማቸው አጥናፍ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous article“ከተዘጉ ፋብሪካዎች ወደ ምርት ትንሣኤ”
Next article“የታሪክ ተወቃሽ ላለመኾን ከጓደኞቼ ጋር የሰላም አማራጭን ተቀብያለሁ” ብሬኑን ይዞ ሰላምን የመረጠው ወጣት