
ኢትዮጵያውያን የተደራጀ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ሳይኖራቸው የሀገራቸውን ዳር ድንበር አስጠብቀዋል፤ ጠላትን በቁርጠኝነት ተዋግተዋል፤ ወራሪ ኀይልን ድባቅ መትተው የነጻነት ተምሳሌት፣ የአፍሪካ ኩራት እና ብርሃን ኾነዋል።
የሀገር መከላከያ ሠራዊት ከተደራጀ በኋላም የውስጥ አንድነቷን በማስጠበቅ፤ ዳር ድንበሯን በማስከበር፤ ሉዓላዊነቷን በማረጋገጥ የመከላከያ ሠራዊት በመስዋዕትነት ኢትዮጵያን እያጸና ነው።
ኢትዮጵያ ባለፉት ዘመናት የተዋቀረ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቢኖራትም ዘመኑን የሚመጥን ቴክኖሎጅ ግን ሳይታጠቅ ቆይቷል። በቅርብ ዓመታት መንግሥት በወሰደው ቁርጠኛ ሪፎርም የመከላከያ ሠራዊት ተቋም በቴክኖሎጅ ታግዞ የሉዓላዊነት አስተማማኝ ዘብ ኾኗል።
በሳይበር ደኅንነት፣ በወታደራዊ ጤና ጥበቃ፣ በአየር ኀይል እና በኤሌክትሮኒክስ ውጊያ ዘርፎች ላይ ውጤታማ ተግባርን ለማከናወን ቴክኖሎጅን በስፋት እየተጠቀመ ነው። ውጤታማነትን ለማጠናከረም ከኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በጋራም እየሠራ ይገኛል።
የምድር ተምዘግዛጊ ንቁ ኀይሎች፤ በጥቅሻ የሚግባቡ፤ ግዳጅን በንሥር ፍጥነት የሚፈጽሙ፤ ለጠላቶቿ ምትኀት የኾኑ ሥልጡን ወታደሮችን በሥሩ አቅፎ ይዟል።
ትናንት በጎራዴ እና በጋሻ የተጠበቀች ሀገር ዛሬ ደግሞ በጠላት ላይ በንሥር ዕይታ ጥቃት የሚሠነዝሩ ኀይሎችን ፈጥራለች። የባሕር ኀይልን መልሶ በማቋቋም ቀጣናዊ ተደራሽነቷን ለማስፋት ሠርታለች። ማንሠራራቷንም አሳይታለች።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ከሀገሩ አልፎ የቀጣናውን ሰላም ለማስከበር በቁርጠኝነት እየሠራ ይገኛል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ኢትዮጵያ የጦር መሳሪያ ከመሸመት ወደ ማምረት ተሸጋግራለች ብለዋል። የተለያዩ የጦር መሣሪያዎችን በማምረት ለገቢያ ለማቅረብ እየሠራች መኾኑንም ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ስጋት የለባትም፤ ጀግና፤ የሠለጠኑ እና ንቃተ ሕሊና ያላቸው የሠራዊት አባላት አሏት ነው ያሉት። መከላከያ ሠራዊት የሚያስፈልገውን ግብዓት በራሱ እያመረተ መኾኑንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እንኳን ዛሬ ትናንትም አልተሸነፈም፤ አሁን ያለበት ቁመና ለሽንፈት ቀርቶ ለሙከራም የሚያሳስብ በመኾኑ እኛን ከመሞከራችሁ በፊት ደጋግማችሁ አስቡ ነው ያሉት።
ዘጋቢ:- ያየህ ፈንቴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
