ወጭ እና ገቢን በማጣጣም የተረጋጋ የፋይናንስ አሥተዳደር መፍጠር ተችሏል።

21
የአማራ ክልል ገንዘብ ቢሮ የክልሉን የ25 ዓመት አሻጋሪ ዕድገት እና የዘላቂ ልማት ግብ መሠረት በማድረግ የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ ከባለድርሻ አካላት ጋር አካሂዷል።
በመድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ገንዘብ ቢሮ ኀላፊ አታላይ ጥላሁን እንደገለጹት የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የተሻለ ውጤት የተመዘገበበት ነበር።
👉በግምገማው የተነሱ ጥንካሬዎች፦ በክልሉ የነበረው የሰላም ሁኔታ የታሰበውን ገቢ ለማሠባሠብ እንቅፋት ቢኾንም ተቋማት ፈተናዎችን በመቋቋም ገቢ መሠብሠብ መቻላቸውን ጠቁመዋል። በዚህም ወጭ እና ገቢን በማጣጣም የተረጋጋ የፋይናንስ አሥተዳደር እንዲፈጠር ተደርጓል።
በበጀት ዓመቱ በመንግሥት በጀት እና በአጋር ድርጅቶች በኩል የፋይናንስ አቅርቦቱን በማሳደግ በርካታ የልማት ሥራዎችን ማከናወን ተችሏል ብለዋል።
ከተለያዩ ተቋማት ጋር በተደረጉ የትብብር ስምምነቶች 18 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ሀብት ለክልሉ መንግሥት ገቢ የተደረገ ሲኾን ይህም ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በእጅጉ ላቅ ያለ አፈጻጸም መኾኑን አቶ አታላይ ጠቁመዋል።
የልማት የፋይናንስ አቅርቦት በመንግሥት በጀት ብቻ የሚሳካ ባለመኾኑ በበጀት ዓመቱ 25 ቢሊዮን ብር ከኅብረተሰቡ መሠብሠብ ተችሏል።
የክልሉን የፋይናንስ መረጃ በዲጂታል ሥርዓት በማደራጀት ግልጽ፣ ቀልጣፋ እና ተደራሽ የሂሳብ አሠራር ተዘርግቷል። ከዚህ ቀደም የዲጂታል ፋይናንስ ተጠቃሚ ያልነበረውን የገጠር ማኅበረሰብ አካታች በማድረግ የብድር አቅርቦት እንዲሳለጥ እና ኅብረተሰቡ ያለማስያዣ የብድር ተጠቃሚ እንዲኾን ማድረግ መቻሉንም ገልጸዋል።
እንደ ቢሮ ኀላፊው ገለጻ የበጀት አሥተዳደር፣ የፋይናንስ ግልጸኝነት እና ተጠያቂነት አሠራርን በማስፈን ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል፤ ዘመኑን የዋጀ የኤሌክትሮኒክስ ግብይት ሥርዓት እንዲኖር ታስቦ የመንግሥት ግዥ እና ንብረት አሥተዳደር አዋጅ እና መመሪያዎች ተሻሽለው ተዘጋጅተዋል።
👉በግምገማው የተመላከቱ ክፍተቶች፦በ2018 በጀት ዓመት የካፒታል ፕሮጀክቶች አፈጻጸም ዝቅተኛ እንደነበር የጠቆሙት አቶ አታላይ በክልሉ ተጀምረው ያልተጠናቀቁ እና የተቋረጡ ፕሮጀክቶች መኖራቸውን ተናግረዋል። እነዚህን ፕሮጀክቶች በ2019 በጀት ዓመት ግንባታቸው እንዲጠናቀቅ በልዩ ትኩረት እንደሚሠራም ገልጸዋል።
ቢሮው በ2019 በጀት ዓመት የክልሉን የውስጥ ገቢ አቅም ለማሳደግ እና የገቢ አሠባሠብ ሥርዓቱን ለማጠናከር፣ የመንግሥት ገንዘብ እና ንብረት አጠቃቀምን በጥብቅ ለመከታተል የሕዝብ ሀብት ለታለመለት የልማት እና የኢኮኖሚ ዕድገት ብቻ እንዲውል ትኩረት አድርጎ እንደሚሠራ ተመላክቷል።
ዘጋቢ፦ ቴዎድሮስ ደሴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous articleተፈጥሮን በመጠበቅ የገቢ ምንጭ ማድረግ ተችሏል።
Next articleበክልሉ ከ108 ሺህ በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ሊገነቡ ነው።