የጳጉሜን ቀናት “የኢትዮጵያ ማንሠራራት” በሚል ስያሜ ይከበራሉ።

12
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት የ2018 ዓ.ም የጳጉሜን ቀናትን ስያሜ እና አከባበር አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።
መግለጫውን የሰጡት የአገልግሎቱ ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ደሲሳ ኢትዮጵያ ካሏት ልዩ ቀናት መካከል የጳጉሜን ቀናት ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል።
የጳጉሜን ወር ያለፈውን ዓመት ሥራዎቻችንን የምንገመግምበት፤ የሚቀጥለውን ዓመት ዕቅድ እና ተስፋም የምንሰንቅበት ልዩ ወር ስለመኾኑም አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ የጳጉሜን ወር ቀናትን በልዩ ስያሜ እያከበረች ነው። ይሄም ዜጎች የግል ዕቅዳቸውን ከሀገራዊ አቅጣጫ ጋር በማስተሳሰር ለሀገር ልማት የበኩላቸውን እንዲወጡ የሚያነሳሳ ነው ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው።
በዚህ ዓመትም አምስቱም የጳጉሜን ቀናት በጋራ “የኢትዮጵያ ማንሠራራት” በሚል መሪ ቃል ይከበራሉ ነው ያሉት። ይህም በእርግጥም የኢትዮጵያን ማንሠራራት የሚያሳዩ ተጨባጭ ለውጦች የተመዘገቡበት ለመኾኑ ማሳያ ነው። ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተጠናቀቀበት፣ ግዙፉ የቢሾፍቱ አየር ማረፊያ የተጀመረበት እና ሌሎችም ዐበይት ስኬቶች የተመዘገቡበት ዓመት ስለመኾኑም ለአብነት አንስተዋል።
እያንዳንዱ ቀናት የራሳቸው ስያሜ ተሰጥቷቸው የሚከበሩ ሲኾን በዚህም መሠረት፦
👉 ጳጉሜን 01፦ የእምርታ ቀን ኢትዮጵያ ከአዝጋሚ ጉዞ ተላቅቃ ወደ ፈጣን የኢኮኖሚ እምርታ ምህዋር መግባቷን የምናሳይበት ቀን ነው።
👉 ጳጉሜን 02፦የማንሠራራት ቀን ኢትዮጵያ ወደሁለንተናዊ ከፍታ ጉዞዋን የጀመረችበት ዓመት በመኾኑ የተሰየመ ነው። ሀገራችን ከጎታች የእድገት ማነቆዎች ተላቅቃ ወደ የማንሠራራት ጉዞዋን ያፋጠነችበት ዓመት ለመኾኑም ማሳያ ነው።
👉 ጳጉሜን 03፦ የጽናት ቀን፦ ኢትዮጵያ በረጅም ታሪኳ በርካታ ፈተናዎችን አሳልፋለች፤ ነጻነት እና ሉዓላዊነቷንም በጽናት አስጠብቃ ኖራለች።
ይህንን ጽናት ማስቀጠል የዛሬው ትውልድም ኀላፊነት መኾኑን ለማስገንዘብ ነው ቀኑ “የጽናት ቀን” ተብሎ የሚከበረው። በቀኑም ከጥዋቱ 12:00 ላይ በመላው ኢትዮጵያ እና በኢምባሲዎችም ጭምር በሁሉም የመንግሥት እና የግል ተቋማት የኢትዮጵያ የሉዓላዊነት ምልክት የኾነውን ሰንደቅ አላማ ከፍ በማድረግ ብሔራዊ መዝሙር ይዘመራል ብለዋል።
👉 ጳጉሜን 04፦ የኅብር ቀን ኢትዮጵያ የብዝኀ ማንነቶች ሀገር ናት፤ ብዝኀነት ኅብረታችን እና ጌጣችን ነው፤ የኃይላችን እና የጥንካሬያችንም ምንጭ ነው። ለዚህም ቀኑ የኅብር ቀን ተብሎ ተሰይሞ ይከበራል። በቀኑ የተለያዩ የበጎ አድራጎት ሥራዎች ይከናወናሉ።
👉 ጳጉሜን 05፦ የነገ ቀን ይህ ስያሜ ኢትዮጵያ ነገን ዛሬ ላይ ኾና የምትሠራ ሀገር መኾኗን መልዕክት ለማስተላለፍ ነው። ነገን ለመገንባት ዛሬን በጥንካሬ መሥራት እንደሚያስፈልግም ማሳያ ነው ብለዋል።
ዘጋቢ፦ አሚናዳብ አራጋው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous articleከ580 በላይ ኢንዱስትሪዎች ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬን አስቀርተዋል።
Next article“ፍትሐዊ የግብር ሥርዓትን ለማረጋገጥ ተሠርቷል”