ከ580 በላይ ኢንዱስትሪዎች ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬን አስቀርተዋል።

4
የአማራ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ያለፈውን ዓመት አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ አካሂዷል።
የቢሮው ኀላፊ እንድሪስ አብዱ ክልሉ በማዕድን፣ በግብርና እና በሰው ኃይል ለኢንቨስትመንት ምቹ እና ሰፊ አቅም ያለው መኾኑን ገልጸዋል።
ቢሮው ነባር ማነቆዎችን ለመፍታት እና አሠራርን ለማዘመን፣ አዳዲስ የአሠራር ማዕቀፎችን በማዘጋጀት ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ ትኩረት መስጠቱንም አስታውቀዋል።
ቢሮ ኀላፊው እንዳሉት ባለፈው በጀት ዓመት:-
✍️ 3 ሺህ 961 አዳዲስ ባለሀብቶች 553 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ካፒታል አስመዝግበዋል።
✍️ 174 መካከለኛ እና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች እና 306 ሌሎች ፕሮጀክቶች ምርት እና አገልግሎት ጀምረዋል።
✍️ የአምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከነበረበት 59 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 65 በመቶ አድጓል።
✍️ ከሥልጠና ተቋማት ጋር በመቀናጀት 2 ሺህ 516 የሠለጠኑ ባለሙያዎች ለአምራች ኢንዱስትሪው ቀርበዋል።
✍️ 583 አምራች ኢንዱስትሪዎች 789 ሺህ 948 ቶን ምርት በማምረት 1 ቢሊዮን 25 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ወጪን ማስቀረት ችለዋል።
✍️ ከ45 በላይ አምራች ኢንዱስትሪዎች እና 6 የሆርቲካልቸር አልሚዎች 206 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር አስገኝተዋል።
✍️ ከ100 ሺህ በላይ ለሚኾኑ ዜጎች (ከዚህ ውስጥ 83 ሺህ 243 ቋሚ) የሥራ ዕድል ተፈጥሯል። በሥራ አፈጻጸሙ ሂደት ያጋጠሙ ማነቆዎችንም ጠቁመዋል።
በቦርድ የተወሰኑ ውሳኔዎች ወደ ታች ወርደው በተግባር ሳይተረጎሙ በየመዝገቡ ላይ መቅረት፣ በተቋማት መካከል ዘላቂ እና የተቀናጀ አሠራር አለመኖር፣ በየደረጃው ላሉ ፕሮጀክቶች በቂ ባለሙያ መድቦ የቅርብ ድጋፍ አለማድረግን ጠቁመዋል።
የዘንድሮው ዕቅድ ከፍተኛ ግብን መነሻ አድርጎ መዘጋጀቱንም ገልጸዋል። የዕቅዱ ዋና ግብ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና እና በማዕድን ዘርፎች ምርት እና ምርታማነትን ማሳደግ እንደኾነ ነው የተናገሩት። ይህን ለማሳካት ከፍተኛ ዲሲፕሊን እና የቅርብ ክትትል ያስፈልጋል ነው ያሉት።
የአገልግሎት ብልሽት የክልሉን የኢንቨስትመንት ገጽታ ስለሚያበላሽ መልካም አስተናጋጅነትን መርሕ ማድረግ እንደሚገባም አንስተዋል።
ዘጋቢ፦ ስማቸው አጥናፍ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous articleመሬትን ከይዞታ ማረጋገጫ ወደ ፋይናንስ አቅም ያዘመነው አዲሱ አሠራር።
Next articleየጳጉሜን ቀናት “የኢትዮጵያ ማንሠራራት” በሚል ስያሜ ይከበራሉ።