
የቀድሞው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ወታደራዊ መሪ ሌተናል ጄኔራል ዮሐንስ ገብረ መስቀል ከሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኅን ጋር በነበራቸው ቆይታ ሕገ ወጡ ሕወሃት በሥልጣን ዘመኑ ዘርፈ ብዙ ሰይጣናዊ እና አረመኒያዊ ድርጊት መፈጸሙን ገልጸዋል።
ለዚህ ባሕሪው አንዱ መገለጫም የሀገር ዳር ድንበር ጠባቂ በኾነው ሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት መፈጸሙ ነው ብለዋል። ይህ በኢትዮጵያ የጦርነት ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ትልቅ የሀገር ክደት ስለመኾኑም አብራርተዋል።
ሕገ ወጡ ሕወሃት ሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት የፈጸመው ሁለት ዓላማዎችን ይዞ እንደነበር ያብራራሉ። የመጀመሪያው ከቻለ አዲስ አበባን መቆጣጠር እና ወደ ቀደመ ሥልጣኑ መመለስ ሲኾን ሌላኛው ሙከራው ካልተሳካ ትግራይን የእሳት ማዕበል ማድረግ ነበር ብለዋል።
ሕገ ወጡ ሕወሃት ስርቆት እና ሌብነት በኢትዮጵያ ባሕል ኾኖ እንዲያድግ ሠርቷል፤ ይህ የቡድኑ መለያ ምልክት ነው፤ በሀገር እና በዜጎች ላይ ምን ያህል ግፍ እና በደል ሲፈጽም እንደነበር ዛሬ ላይ ጊዜ ዳኛ ኾኖ ምስክር እየሰጠ ስለመኾኑም ሌተናል ጄኔራሉ አንስተዋል።
የትግራይ ወጣቶችን በየጊዜው ወደ ጦርነት በመማገድ በተወለዱበት እንዳይቀበሩ እና የበርሃ ሲሳይ ኾነው እንዲቀሩ ለዘመናት ሢሠራ ቆይቷል። በተለይም መንታ ማንነት ያላቸው የድርጅቱ ፈላጭ ቆራጮች በትግራይ ሕዝብ ላይ የብቀላ ወንጀል ሲፈጽሙ ቆይተዋል ነው ያሉት።
አሁንም የትላንት ጥፋቱ ሳያንሰው ከሻቢያ እና ሌሎች ኀይሎች ጋር ” ጽምዶ” የሚል ጥምረት ፈጥሮ ኢትዮጵያን ዳግም ለመውጋት እየተንቀሳቀሰ ነው ብለዋል።
በዚህ የጦርነት እንቅስቃሴ የትግራይን ወጣት በግዳጅ እና በአፈሳ ወደ ካምፕ እየወሰደ ስለመኾኑም ጠቁመዋል።
“ጽምዶ” ባለቤቱ የኤርትራው አምባገነን መሪ ኢሳያስ ነው ያሉት ጄኔራል ዮሐንስ ሕገ ወጡ የሕወሃት ቡድን እና ሻቢያ ከጥንት ጀምሮ ውል የለሽ የጥፋት ኃይሎች ስለመኾናቸውም መስክረዋል።
ሌተናል ጄኔራል ዮሐንስ ገብረመስቀል ለመገናኛ ብዙኅን በተደጋጋሚ እንደገለጹት የጥፋት ጥምረቱ በታሪካዊ ጠላቶች በሚሰፈርለት ቀለብ ልክ የሚያሰራጨው ስሁት ፕሮፓጋንዳ ሕዝብን እያወናበደ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
በመኾኑም ሕገ ወጡ የሕወሃት ቡድን ከምሥረታው ጀምሮ እስካሁን በሀገር እና በሕዝብ ላይ ያደረሰውን ሰይጣናዊ እና አረመኔያዊ ግፍ ለቀጣዩ ትውልድ ትምህርት ይኾን ዘንድ ታሪኩን የሚያስታውስ ሐውልት ሊቆም እንደሚገባ አሳስበዋል።
በትጥቅ ትግል ታግዞ የሚካሄድ ኋላቀር የጠመንጃ እንቅስቃሴ ሀገርን እና ሕዝብን ከመከራ፣ ከውድቀት እና ከማጎሳቆል የዘለለ አንዳች ፋይዳ አለመኖሩን በመረዳት ሁሉም ለሰላም እና ለልማት ዘብ ሊቆም እንደሚገባ ሌተናል ጄኔራሉ አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ ቴዎድሮስ ደሴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
