
የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም ዓቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናልን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) መርቀው ከፍተውታል።
በምረቃ መርሐ ግብሩ መልዕክት ያስተላለፉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ባሕር ዳር ታሪክ እስከ ተፈጥሮ ሳይሰስቱ ውበት ያበዙላት ታሪክ ያጠገባት “የአፍሪካ የልማት፣ የዕድገት እና የብልጽግና ተምሳሌት የምትኾን ከተማ ናት” ብለዋል።
በኢትዮጵያ ሲደረግ ለነበረው የንግድ ሥርዓት መሸጋገሪያ ማዕከል ኾና ስታገለግል የቆየች ብትኾንም ባሕር ዳር በሚገባት የመልማት አቅም ልክ ሳትለማ መቆየቷን ጠቁመዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ቱሪዝምን የሚያነቃቁ በርካታ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
በከተማዋ ሰፊ የኮሪደር ልማት እና የውስጥ ለውስጥ መንገዶች እየተሠሩላት መኾኑን ነው የገለጹት። የባሕርዳር ዓለም አቀፍ ስታዲዬም ግንባታ ሌላው የከተማዋ የልማት ማሳያ ስለመኾኑም አንስተዋል። እነዚህም ወደ አካባቢው ለሚመጡ ሰዎች አስደሳች ሁኔታን የሚፈጥሩ ናቸው ብለዋል።
ዕድል ስናገኝ እንጠቀምበት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ችግርን ወደ ዕድል በመቀየር ለልጆቻችን የሚተርፍ ሥራን መሥራት ልማት እናድርግ ነው ያሉት። ሰላም ውድ ስጦታ፣ ጊዜ ትልቅ ሀብት፣ ስራ ትልቅ ጸጋ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከምንጊዜውም በላይ ለልማት መተባበር እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
