መደማመጥ የችግሮች መፍቻ ቁልፍ

26
📌
ኢትዮጵያ ረጅም ዘመናትን ያስቆጠረ በማኅበራዊ መስተጋብር እና በትውፊት የታነጸ የጋራ እሴት ያላት ሀገር ናት።
ከእሴቶች መካከልም መደማመጥ እና መመካከር ለሀገር ሰላም እና ለአብሮነት ዋነኛ ምሰሶ ኾነው ዘመናትን አገልግለዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህ የመደማመጥ ባሕል እየተሸረሸረ መምጣቱ እና በምትኩ አለመግባባት፣ የሃሳብ መገፋፋት እና አለመቻቻል እየነገሡ መጥተዋል። ይህም ለዘርፈ ብዙ ችግሮች እየዳረገ ይገኛል።
በቀደመው ሥርዓት እና ትውፊት ኢትዮጵያውያን ለሽምግልና፣ ለዕርቅ እና ለምክር ትልቅ ቦታ ይሰጡ ነበር። አባቶች በትልልቅ ዛፍ ስር ወይም በተመረጠ ቦታ ተቀምጠው የቱንም ያህል የከረረ ቂም ቢኖር በንግግር እና በብልሃት ይፈቱትም ነበር።
📜 ታዋቂው የታሪክ ተመራማሪ እና ደራሲ ፕሬፌሰር ባሕሩ ዘውዴ የዘመናዊት ኢትዮጵያ ታሪክ በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ ኢትዮጵያውያን ግጭቶችን በውይይት እና በባሕላዊ የዕርቅ ሥርዓቶች የመፍታት ትልቅ ልምድ እንደነበራቸው ገልጸዋል። ይህም ሽማግሌዎች ጣልቃ የሚገቡት ለይስሙላ ሳይኾን ቃላቸው እንደ ሕግ ይከበር ስለነበር እንደኾነም አንስተዋል። ይህም የሚያሳየው መደማመጥ የባሕል መግለጫ ብቻ ሳይኾን ሀገርን ከትርምስ የሚጠብቅ አቅም የነበረው መኾኑን ነው።
⚠️አሁን ላይ ግን የዲጂታል ሚዲያው መስፋፋት፣ የፖለቲካው መከፋፈል እና የኑሮ ዘይቤው መቀየር የመደማመጥ እሴትን እያሳጣ ይገኛል። ሰው የሚሰማው ለመረዳት ሳይኾን ለመመለስ አልያ ለመንቀፍ እየኾነ ነው።
ደራሲ ዮናስ አድማሱ (ዶ.ር) በአንድ ወቅት የኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር መጽሔት ላይ በሰጡት ቃለ ምልልስ የባሕል መናጋቱን ሲያስረዱ የዘመናችን ትልቅ ቀውስ “እኔ ብቻ ልናገር፣ እኔ ብቻ ልወቅ” ባይነት ነው ብለው ነበር። መደማመጥ በሌለበት ማኅበረሰብ ውስጥ ደግሞ አብሮነት አይኖርም ነው ያሉት።
ይህም አሁን ላይ እየተስተዋለ ላለው ያለመደማመጥ ሁኔታዎች አንዱ ማሳያ ነው። የመደማመጥ ባሕል እየጠፋ በመምጣቱም እርስ በእርስ መጠራጠር እየገነነ መተማመን እየጠፋ መጥቷል።
ልዩነቶችን በጠረጴዛ ዙሪያ በሰላማዊ ውይይት የመፍታት አቅም እያሳጣም ነው። ይህም የጋራ ታሪክን ወደ ጎን በመተው ሀገራዊ አንድነትን ጥያቄ ውስጥ እያስገባው መጥቷል።
በቀደመው ዘመን የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ፈጣሪን ፍሩ፤ ታረቁ ሲሉ የጦር መሣሪያ የያዘ ኀይል እንኳ መሣሪያውን ያወርድ ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የእነሱም ተደማጭነት እየቀነሰ እና ለፖለቲካዊ ጥቅሞች ተጋላጭ የመኾን አዝማሚያ ይስተዋላሉ።
ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን ሀገር ሽማግሌ ስታጣ፣ ወጣት ምክር ሲንቅ፣ ያኔ ሀገር ይናጋል ነበር ያሉት። አሁን ላይ እየኾነ ያለውም ይሄው ነው። ሽማግሌዎች የሀገር የሰላም ሚዛኖች ነበሩ። ናቸውም።
ታዋቂው የመብት ተሟጋች እና ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም “መክሸፍ እንደ …. ታሪክ”በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ ሽማግሌዎችን እና የሃይማኖት አባቶችን ማክበር ያቆመ ትውልድ የራሱን ታሪክ እና መጻኢ ዕድል እያጠፋ ነው፤ ዕውቀት በዕድሜ እና በልምድ ይገነባል፤ እኛ ግን የሽማግሌዎቻችንን ቃል ማቃለል ጀምረናል በማለት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የትውልዱን አለመደማመጥ አመላክተዋል።
💡የቀደመው የኢትዮጵያውያን የመደማመጥ እና የመመካከር ባሕል ለሀገር ሕልውና ጋሻ ነበር። አሁን ላይ እያጋጠሙ ያሉ ቀውሶች መፍትሔያቸው የውጭ ፍልስፍና ሳይኾን ወደ ራሳችን ባሕላዊ እሴቶች መመለስ ነው።
የሃይማኖት አባቶች እና በዕድሜ ገፋ ያሉ አባቶችም ሚናቸውን መልሰው እንዲያገኙ ወጣቱ ትውልድ ደግሞ በትሕትና የመስማትን ጥበብ ሊለማመድ ይገባል።
💬 እርሶስ ምን ይላሉ? የመደማመጥ ባሕላችንን መልሶ እንዲያንሰራራ ከእያንዳንዳችን ምን ይጠበቃል? አስተያየትዎን በሀሳብ መስጫ ሳጥኑ ውስጥ ያጋሩን 👇
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous article4ሺህ ድምጾች በኢትዮጵያ የንጋት ወጋገን ላይ…
Next articleችግኞችን ከመትከል ባሻገር ለጽድቀት በልዩ ትኩረት እየተሠራ ነው።