
ኢትዮጵያ እየመከረች ነው። ሀገራዊ ምክክሩን በማስመልከት አስተያየታቸውን ለአሚኮ የሰጡ የሰቆጣ ከተማ ነዋሪዎች ሀገራዊ ምክክሩ ኢትዮጵያን የሚያክም ፍቱን መድኃኒት እንደሚኾን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
በሀገር ሽማግሌነት የሚያገለግሉት ዲያቆን ገበያው ኪሮስ እና አቶ ገበያው ደረበ እንደገለጹት ምክክር እና ሽምግልና ቂም በቀልን የሚያስወግድ የኖረ ጠብን የሚያሥረሳ ትልቅ ገመድ ነው ብለዋል።
እንደ ሀገርም እየተደረገ ያለው ምክክር ኢትዮጵያውያን እየመከሩ ለችግሮች መፍትሄ የሚያመጡበት ይኾናል ያሉት ሽማግሌዎቹ በመመካከር የማይፈታ ችግር እና የማይድን ቁስል አይኖርም ነው ያሉት።
የሰቆጣ ከተማ ነዋሪዎቹ ወይዘሮ ኤልሳ ጆርጅ እና ወይዘሮ ምሥራቅ ተድላ ሀገራዊ ምክክሩ ሰላምን በመፍጠር አንድነትን ይፈጥራል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል።
በጦርነት፣ በመለያየት እና በመጣላት ሀገር እንደማትጸና ባለፉት ዓመታት አይተናል ያሉት አስተያየት ሰጭዎቹ ምክክሩንም በንቃት እየተከታተሉት እንደሚገኙ ነው ያብራሩት።
እንደ ዋግ ሕዝብም የሀገርን ሰላም ለማጽናት ከጸጥታ መዋቅሩ ጋር እየሠሩ መኾናቸውንም አክለው ጠቅሰዋል።
#አሚኮ #ሀገራዊ_ምክክር #ኢትዮጵያ
#ሰቆጣ፡ ሐምሌ 09/2018 ዓ.ም
ዘጋቢ- ደጀን ታምሩ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
