
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሀገራዊ የምክክር ጉባኤውን እያካሄደ ነው። በምክክር ጉባኤው መክፈቻ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) እና ሌሎችም ከፍተኛ መሪዎች እንዲሁም የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች ተገኝተዋል።
በምክክር ጉባኤው ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ መልእክት ያስተላለፉት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ እንዳሉት ምክክሩ ጠንካራ እና አስተማማኝ ሀገር ለመገንባት አዲስ ምእራፍ የሚከፍት ነው ብለዋል። የኢትዮጵያን ታላቅነት ለማስቀጠል እንቅፋት የሚኾኑ ጉዳዮችን ለመፍታትም ያገለግላል ነው ያሉት።
ጉባኤው የሀገራችንን የኢኮኖሚና ፖለቲካዊ የጉዞ አቅጣጫ የሚያቀና፣ ለቀጣዩ ትውልድም ጠንካራ እና አስተማማኝ ሀገር ለመገንባት የሚያስችል አዲስ ምእራፍ ከፋች ነው ብለውታል።
የኢትዮጵያን ታላቅነት ለማስቀጠል እንቅፋት የሆኑ በርካታ አለመግባባቶች የዜጎችን እና የሀገርን ሰላም እየፈተኑ ይገኛሉ። እነዚህን ስር የሰደዱ ችግሮች በኀይል ጊዜያዊ ማስታገሻዎች ሳይኾን በምክክር መፍታት ይገባል ነው ያሉት። ግልጽ፣ ታማኝ እና ሳይንሳዊ ሀገራዊ ምክክር ማድረግም ወሳኝ መኾኑን አመላክተዋል።
