
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 29/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ በፍልሰት አሥተዳደር እና አሠራር ሥርዓት መወሰኛ ደንብ ቁጥር 252/2018 ዙሪያ ከሚመለከታቸው አጋር እና ባለ ድርሻ አካላት ጋር መክሯል።
የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ ኀላፊ ብርሃኑ ጎሽም በሰው የመነገድ፤ ሰውን በሕገ ወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር እና ለሥራ ወደ ውጭ ሀገር መላክ ወንጀሎች በዜጎች ላይ ዘርፈ ብዙ ጉዳቶችን እያስከተለ ነው ብለዋል።
ችግሩን በዘላቂነት ለመቆጣጠር የፍልሰት አሥተዳደር እና አሠራር ሥርዓት መወሰኛ ደንብ ተዘጋጅቶ በክልሉ መሥተዳድር ምክር ቤት መጽደቁን አስታውቀዋል።
በፍልሰት ምክንያት በዜጎች ላይ እየደረሱ ላሉ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ምላሽ በመስጠት ወንጀሉን ለመከላከል የተቋማትን ቅንጅት የሚጠይቅ መኾኑንም አንስተዋል። ለዚህም በትብብር መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል።
የአማራ ክልል ሥራ እና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኅላፊ ምሳዬ መኮንን እስካሁን የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ በርካታ ወጣቶች ለሥራ ፍለጋ በደላሎች እየተታለሉ ችግር ሲደርስባቸው መቆየታቸውን ገልጸዋል።
በደንቡ መሠረት ተቋማት በትብብር ከሠሩ በተለይም ለወጣቶች ጠቀሜታው የጎላ መኾኑን ተናግረዋል። በአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ የሕግ ምርምር ማርቀቅ እና ማጠቃለል ዳይሬክተር ፀሐይነህ አጥናፍ ደንቡ ተቋማት ተናበው በቅንጅት እንዲሠሩ ታስቦ የወጣ ነው ብለዋል።
ግንዛቤ በመፍጠር፤ ተጎጂዎችን በማቋቋም፤ ጥናት እና ምርምር በማድረግም በኢኮኖሚ አቅማቸው የሚገነባበት አሠራርን መሠረት ያደረገ መኾኑን አብራርተዋል።
ይህንን የሚመሩ ተቋማትም ተግባሩን እንደ አንድ የሥራ መለኪያ አድርገው የሚሠሩበት ነው ብለዋል። ተግባሩን በማይፈጽሙ ተቋማት ላይ ተጠያቂነት እንደሚኖር አስገንዝበዋል።
ዘጋቢ: አሰፋ ልጥገበው
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !
See less
