የመንግሥት ሠራተኞችን መረጃ የማጥራት እና በዲጂታል የማደራጀት ሥራ ወሳኝ ነው።

5
ደብረብርሃን: ሚያዚያ 12/2018 (አሚኮ) በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሚገኙ ሠራተኞችን አጠቃላይ መረጃ በዲጂታል ሥርዓት ለማስመዝገብ እና የመረጃዎቹን ትክክለኛነት የማረጋገጥ ሥራ በመጭው ሚያዚያ 23/2018 ዓ.ም እንደሚጀመር የአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ አስታውቋል።
ቢሮው ለዚህ ተግባር ስኬታማነት የሚያግዝ የአቅም ግንባታ ሥልጠና በደብረ ብርሃን ከተማ እየሰጠ ነው።
ሥልጠናው በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት እና በፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ትብብር የተዘጋጀ መኾኑ ተጠቁሟል።
አዲሱ የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ከጸደቀ በኋላ አፈጻጸሙን የሚያግዙ ስትራቴጂዎች እና መመሪያዎች ተዘጋጅተው ወደ ሥራ መገባቱን የአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ የአደረጃጀት፣ የሥራ ምዘና እና ክፍያ ጥናት ዳይሬክተር አንተነህ ይስማው ተናግረዋል።
የሥራው ዋነኛ ዓላማ የሠራተኛውን መረጃ በአንድ ማዕከላዊ ቋት ውስጥ በማደራጀት ያለውን የሰው ኀይል ከሚሰጠው አገልግሎት እና ከተገልጋዩ ፍላጎት ጋር በቅንጅት ለማጣመር መኾኑን አንስተዋል።
የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ ወርቃለማሁ ኮስትሬ የዲጂታላይዜሽን ተግባሩ የጠራ እና የተደራጀ መረጃ እንዲኖር ከማድረጉ ባለፈ ትክክለኛውን አገልግሎት ሰጭ ለመለየት እና አሠራሩን ግልጽ ለማድረግ ትልቅ አጋዥ መኾኑን ገልጸዋል።
ይህ የመረጃ ማረጋገጫ ርምጃ የሠራተኞችን የትምህርት ዝግጅት፣ የሥራ ልምድ እና አገልግሎት ዘመን መሠረት በማድረግ ለየሥራ ዘርፎቹ የሚያስፈልገውን ትክክለኛ የሰው ኀይል በአግባቡ ለመለየት እንደሚያስችል ተመላክቷል።
ሥራው በሚጀመርበት ቀን ሁሉም የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሠራተኞቻቸውን መረጃ ጥራት የማረጋገጥ እና ወደ ዘመናዊው ሥርዓት የማሸጋገር ተግባር በትኩረት ያከናውናሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ዘጋቢ፦ብርቱካን ማሞ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !
Previous articleኢትዮጵያ ያደረገችው የኢኮኖሚ ሪፎርም የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት አንዲያድግ አድርጓል።