
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ሕዝብ የመሠረተ ልማት ጥያቄ የሚያነሳ ብቻ ሳይኾን ልማቶች እንዲከናወኑ ድጋፍ የሚያደርግ መኾኑን የአማራ ክልል ከተማ እና መሠረተ ልማት ቢሮ አማካሪ ሽቤ ክንዴ ገልጸዋል።
ከኮሪደር ልማት ውጭ በአሁኑ ወቅት በክልሉ 728 ከተሞች ላይ የሚተገበሩ 995 የከተማ ልማት ፕሮጀክቶች ይገኛሉ ብለዋል።
ብዙዎቹ እየተተገበሩ የሚገኙት በኅብረተሰቡ አቅም ነው። 52 በመቶው በማኅበረሰቡ እና 48 በመቶው ደግሞ በመንግሥት ወጭ እንደሚገነባም አንስተዋል።
“በመንግሥት በጀት ብቻ ከተማ ሊለማ አይችልም” ያሉት አቶ ሽቤ ወደፊትም ያለውን ሰፊ የማኅበረሰብ አቅም በማደራጀት ለመጠቀም ይሠራል ነው ያሉት።
በኮሪደር ልማትም የማኅበረሰቡ ተሳትፎ ከፍተኛ መኾኑን ነው የተናገሩት። እስካሁን መንግሥት 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ለኮሪደር ልማቱ አውጥቷል ብለዋል።
ከኅብረተሰቡ ደግሞ 5 ቢሊየን ብር ለመሠብሠብ ታቅዶ 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ተሠብሥቧል ነው ያሉት።
መሠረተ ልማቶች ከፍተኛ ገንዘብ ወጥቶባቸው የሚከናወኑ ናቸው፤ መሠረተ ልማቶች ጉዳት ሲደርስባቸው እና አገልግሎት ሲቋረጥ በማኅበረሰቡ ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ መቃወስ ይፈጥራሉ ነው ያሉት።
በመኾኑም ልማቶችን ለመጠበቅ የተለያዩ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማት ለማኅበረሰቡ ጥቅም እና ለትውልድ የሚሻገር ሥራ ስለኾነ ኅብረተሰቡ መሳተፍ እንዳለበትም አስገንዝበዋል። ልማቶችን መጠበቅ እንዳለበትም አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ አድኖ ማርቆስ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
