‎በሰሜን ሸዋ ዞን የግሪሳ ወፍ ሰብል እንዳይጎዳ በአውሮፕላን የታገዘ የኬሚካል ርጭት እየተከናወነ ነው።

4

‎በዞኑ ስምንት ወረዳዎች የግሪሳ ወፍ መከሰቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል።

‎በአማራ ክልል የሰሜን ሸዋ ዞን ግብርና መምሪያ ኀላፊ ታደሰ ማሙሻ ለአሚኮ እንደተናገሩት ክስተቱ ባጋጠማቸው አካባቢዎች የመከላከል ሥራ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል።

‎የግሪሳ ወፍ የተከሰተባቸው አካባቢዎች፦ ቀወት፣ አንፆኪያ ገምዛ፣ ኤፍራታና ግድም፣ በረኸት፣ አንኮበር፣ ጣርማበር፣ ምንጃር ሸንኮራ ወረዳዎች እና ሸዋሮቢት ከተማ አሥተዳደር ናቸው።

‎ይህንን ተከትሎ የመከላከል ሥራ እየተከናወነ ሲኾን በአውሮፕላን የታገዘ የኬሚካል ርጭት በመካሄድ ላይ ነው ብለዋል ኀላፊው።

‎እስከአሁን በአንፆኪያ ገምዛ ወረዳ ሁለት የግሪሳ ወፍ ማደሪያ ጣቢያዎች ላይ ርጭት ተደርጎበታልም ነው ያሉት።

‎በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ የተከሰተውን ግሪሳ ለመከላከል ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመነጋገር ርጭት ለመጀመር ዝግጅት ስለመደረጉም አብራርተዋል።

‎የግብርና ተቋማት መሪዎች እና ባለሙያዎች አስፈላጊውን ስምሪት ወስደው ግሪሳውን በመከላከል ላይ ናቸው ብለዋል።

‎ክስተቱ ባለባቸው ሁሉም ወረዳዎች የኬሚካል ርጭት ለማካሄድ የአቅጣጫ ጠቋሚ ሥራዎች ተሠርተው ስለመጠናቀቃቸውም አስገንዝበዋል።

‎ክስተቱ ባጋጠመባቸው አካባቢዎች ርጭቱ እስኪደርስ ሁሉም አርሶ አደሮች ወፉ አርፎ ሠብል ላይ ጉዳት እንዳያደርስ በባሕላዊ መንገድ መከላከል እንደሚገባም መልዕክት አስተላልፈዋል።

‎#አሚኮ #የግሪሳወፍ_መከላከል #አማራክልል
‎#ኢትዮጵያ 🇪🇹

‎#ባሕር_ዳር #መስከረም_09_2019_ዓ_ም

‎ዘጋቢ፦ ኤልያስ ፈጠነ

‎የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

Previous articleከሞት ስጋት ወደ ተረጋጋ ሕይወት!_ የምዕራብ ጎጃም ዞን የሰላም ተስፋ