በአማራ ክልል ከ 1 ሺህ 200 በላይ ለሚኾኑ ታራሚዎች ይቅርታ ተደረገ።

13
የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ ኀላፊ ብርሃኑ ጎሽም በ 2019 አዲስ ዓመት በክልሉ ይቅርታ የተደረገላቸውን ታራሚዎች አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸውም የክልሉ መሥተዳደር ምክር ቤት ጳጉሜ 4/2018 ዓ.ም ባካሄደው ሰባተኛ ዙር አንደኛ ዓመት የሥራ ዘመን አንደኛ አስቸኳይ ስብሰባ የክልሉ ፍትሕ ቢሮ በሁለተኛ ዙር ይቅርታ ሊደረግላቸው ይገባል የተባሉ የሕግ ታራሚዎችን አስመልክቶ ባቀረበው የውሳኔ ሀሳብ ላይ ተወያይቶ ውሳኔ መስጠቱን ተናግረዋል።
በዚህ መሠረትም ወንድ 1 ሺህ 169፤ ሴት 33 በድምሩ 1 ሺህ 202 ታራሚዎች ከጳጉሜ 4/2018 ዓ.ም ጀምሮ በይቅርታ እንዲፈቱ የክልሉ መሥተዳደር ምክር ቤት ወስኗል ነው ያሉት።
የይቅርታ ተጠቃሚ የኾኑ ታራሚዎች ይቅርታውን ሊያገኙ የቻሉባቸውን ምክንያቶች ሲጠቅሱ፦
✅ በመመሪያው መሠረት መጨረስ ያለባቸውን ፍርድ አጠናቅቀው የተገኙ፤
✅ እርቅ በሚጠይቁ ወንጀሎች ላይ ከተበዳይ ወገን ጋር እርቅ የፈጸሙ መኾናቸው የተረጋገጠ፤
✅ ለተበዳይ ወገን በደረሰባቸው ጉዳት ልክ ካሣ መካስ የቻሉ፤
✅ በሕክምና የማይድን የጤና ችግር ያለባቸው ታራሚዎች ከማረሚያ ቤት ውጪ ኾነው ጤናቸውን እንዲከታተሉ በመረጋገጡ፤
✅ ለፍርዱ ምክንያት የኾነው ወንጀል በሕግ መሠረት ይቅርታ የሚያሰጥ መኾኑ የተረጋገጠ
✅ በማረሚያ ቤት ቆይታቸው ከጥፋታቸውን የተጸጸቱ፣ የባሕሪ ለውጥ ያመጡ እና የታረሙ ለመኾናቸው ማረጋገጫ የቀረበላቸው፤
✅ መሥተዳደር ምክር ቤቱ ይቅርታ ቢሰጣቸው ኅብረተሰቡ ውስጥ ገብተው ሰላማዊ ኑሮ ይኖራሉ ብሎ ያመነባቸው ታራሚዎች ናቸው ብለዋል።
ከተበዳይ ወገን ጋር እርቅ መፈጸም ያልፈለጉ፤ ለተበዳይ ወገን ካሣ ለመክፈል ፈቃደኛ ያልኾኑ፤ የእሥራት ቅጣታቸውን ያልጨረሱ እና በጾታዊ ጥቃት ተከሰው ፍርድ ያገኙ ታራሚዎች የይቅርታው ተጠቃሚ አልኾኑም ነው ያሉት።
የክልሉ መሥተዳደር ምክር ቤት በጸጥታ ችግር ውስጥ ኾኖም ይህን ውሳኔ ማሳለፉ ለዜጎች መብት ጥበቃ ያለውን አርቆ አሳቢነት ያሳየ ነው ብለዋል። በተጨማሪም ሰዎች ከጥፋታቸው መማር የሚችሉ መኽናቸውን ከግንዛቤ ውስጥ ያስባ መኾኑን ገልጸዋል።
የክልሉ መንግሥት ይቅርታ የተደረገላቸው ታራሚዎች ወደ ኅብረተሰቡ ሲገቡ ለክልሉ ሰላም እና ደኅንነት መረጋገጥ የራሳቸውን ሚና እንደሚወጡ እምነት አሳድሮ የይቅርታ ተጠቃሚ እንዲኾኑ ውሳኔ ማስተላለፉን ተናግረዋል።
በይቅርታ ወደ ኅብረተሰቡ የሚቀላቀሉ ታራሚዎች በርግጥም የታረሙ እና የባሕሪ ለውጥ ያመጡ መኾናቸውን ለክልሉ ሰላም መረጋገጥ በመሥራት፤ የወንጀል አስከፊነትን በማስተማር እና በሌሎች በጎ ተግባራት በመሳተፍ ማሳየት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ አድኖ ማርቆስ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
Previous articleየኢኮኖሚ ካቴናውን መበጠስ ለነገው ትውልድ የነጻነት ስንቅ ነው።
Next articleእንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሳችሁ፣ አደረሰን!!