
የ21ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በዓል አከባበር መሪ ዕቅድ ውይይት በፌዴሬሽን ምክር ቤት አዘጋጅነት እየተካሄደ ነው።
የውይይት መድረኩን የከፈቱት የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር በየዓመቱ የሚከበረው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን ኅብረ ብሔራዊ አንድነትን በማጠናከር ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
21ኛው በዓል የሕዝቦችን መተዋወቅ እና ጠንካራ ሀገረ-መንግሥት ግንባታን በተግባር የምናሳይበት ታሪካዊ መድረክ ነውም ብለዋል። ቀኑ ልዩ እና ታሪካዊ ትርጉም አለው ያሉት አፈ ጉባኤው 7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ በማጠናቀቅ በአዲስ መንግሥት ምሥረታ ማግስት መከበሩ ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።
ከዚህም ባሻገር ኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር አካሂዳ በውይይት ችግሮችን የመፍታት ዴሞክራሲያዊ ባሕልን የጀመረችበት ወቅት ነው፤ በምክክሩም በሕዝቦች መካከል መቀራረብን እና መተዋወቅ በተፈጠረበት ማግስት መከበሩ በዓሉን ልዩ ያደርገዋል ነው ያሉት።
አፈ ጉባኤው በመልእክታቸው ያነሷቸው ዓበይት ጉዳዮች፦
7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ በሰላም በማጠናቀቅ በአዲስ መንግሥት ምሥረታ ማግስት የምናከብረው ታሪካዊ በዓል ነው።
በተጨባጭ በሕዝቦች መካከል አንድነትን በማረጋገጥ ኢትዮጵያ የብሔር፣ ብሔረሰቦች ሀገር መኾኗን አረጋግጠናል።
ባለፉት ዓመታት ያካበትነውን ልምድ እና ያስመዘገብናቸውን ስኬቶች በማካፈል፣ በሕዝብ ለሕዝብ ውይይት ጠንካራ አንድነት እንዲፈጠር በጋራ እንሥራ ብለዋል ዋና አፈ ጉባኤው።
ዘጋቢ፦ ኢብራሂም መሐመድ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
