
ኢትዮጵያ በአንድ ወቅት የዓለምን ሥልጣኔ፣ ንግድ፣ ጅኦ ፖለቲካ፣ ወታደራዊ ኀይል የምትመራ፤ በቀይ ባሕር ላይ በሙሉ የበላይነት የነገሠች ባለ ግርማ ነበረች።
በዚያ ዘመን ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤት ብቻ አልነበረችም። የዓለማችንን ቀጣይ እጣ ፈንታ ወሳኝ፤ በሥልጣኔ፣ በኢኮኖሚ እና በወታደራዊ ልዕልናዋ ተፅዕኖ ፈጣሪ፤ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ነገሥታት እና መንግሥታት በክብር እና በፍርሃት የሚመለከቷት እውነተኛ ኀያል መንግሥት ነበረች እንጅ።
በወቅቱ የነበራት የባሕር ላይ ወታደራዊ አቅም እስከ ቀይ ባሕር የተዘረጋውን ድንበሯን እና ሉዓላዊነቷን ከማስከበር አልፎ የቀይ ባሕር እና የሌሎች የባሕር ድንበርተኛ ሀገራትን ሰላም እና ደኅንነት ሙሉ በሙሉ እስከመቆጣጠር የደረሰ እንደነበር ይነገራል።
ሐሪ አትክንስ የተባለ ጸሐፊ “የኢትዮጵያ ታሪክ” በሚል በጻፈው እና በቀጥታ ወደ አማርኛ በተተረጎመው መጽሐፍ የመጀመሪያው ዝነኛ የአክሱም መንግሥት የነበረው የባሕር በር አዶሊስ ነው። ንጉሥ ካሌብ ጠንካራው የአክሱም ንጉሥ መኾኑን ገልጾ ከሮም፣ ሕንድ እና አውሮፓ ጋር የንግድ ልውውጥ ያደርግ እንደነበር ጽፏል።
ሙንሮ የተባለ አንድ ጸሐፊ ደግሞ “የአክሱም ሥረወ-መንግሥት” በሚል መጽሐፉ እንዳሰፈረው፥ በአክሱም ሥረወ መንግሥት ኢትዮጵያ ወደቧን እና የዳሕላክ ደሴቶቿን የሚቆጣጠሩ ወታደሮች የሚያልፉበት የላቀ የባሕር ላይ ሎጅስቲክስ እና የጦር መርከቦች መሠረተ ልማት እንደነበሯት በሰፊው አስፍሯል።
ይህ መዋቅር እስከ ዘመናዊቷ ኢትዮጵያ ድረስ ዘልቆ 26 ዘመናዊ የጦር መርከቦች፣ የምጽዋና የአሰብ የባሕር ኀይል ጦር ሰፈሮች፣ እና በጥልቅ ወታደራዊ ሳይንስ የሠለጠኑ 3ሺህ 500 የባሕር ኀይል ወታደሮች እንደነበሯትም ይነገራል።
ኢትዮጵያ ኀያል በኾነችበት በዚያ ዘመን እንኳን ከዓለም መንግሥታት ጋር የነበራት ግንኙነት ልክ እንደ አሁኑ ኹሉ በእኩልነት፣ በዲፕሎማሲያዊ ብስለት እና በጠንካራ አጋርነት ላይ የተገነባ ነበር።
ያ የባሕር ላይ የበላይነት እና ወታደራዊ አቅም ግን አብሯት አልዘለቀም። የኢትዮጵያ ኀያል መኾንን ፈጽሞ የማይፈልጉ ኀይላት ከቀይ ባሕር ለማግለል መሥራት የጀመሩትም ከዚያ የኀያልነት ዘመኗ ጀምረው ነበር። ለዚህም ነው መገለሉ በአንድ ጀምበር የመጣ ብቻ አይደለም የሚባለው።
ዘመናት ከፈጀው የጠላቶች ሴራ በኋላ ሕዝቡን እርስ በእርስ እንዳይግባባ በማድረግ፤ ከራሷ አብራክ ኤርትራን በመገንጠል ያቺን የባሕር ላይ ንግሥት ከንግሥናዋ ገፏት። ያኔ የኀያልነቷ ትልቅ ዓምድ እና የኢኮኖሚዋን ዋስትና አጣች።
በዓለም የንግድ መድረክ ላይ ዋጋ የምትወስን፣ የራሷን መርከቦች አሰማርታ በባሕር ላይ እንደልቧ ትሠለጥን የነበረችውን ኀያል ሀገር፥ በቢሊዮን ዶላር እየከፈለች ለዚያውም በሌሎች ርህራሄ እና ፈቃድ ምርት የምታሸጋግር ሀገር አደረጓት። በመጨረሻም ኢኮኖሚዋን በማድቀቅ የድህነት አረንቋ ውስጥ ከተቷት። ከዚያም ራሳቸው “ደሃ ሀገር” የሚል ታርጋ ለጠፉባት።
ቀይ ባሕር የአፍሪካ ቀንድ የሰላም እና የደኅንነት ቁልፍ መኾኑ እየታወቀ ያንን የሰላም ማስከበር ተልዕኮዋን በመንጠቅ በቀጣናው የሚንቀሳቀሱ የሰላም እና ደኅንነት ስጋቶችን ከሩቅ እንዳትመክት አደረጉ። ዓላማቸውም ያ ነበርና ቀጣናውን ራሳቸው ያፈሯቸው አሸባሪዎች መፈንጫ አደረጉት። እንዲያም ኾኖ አሁንም ቀጣናውን ከመጠበቅ ወደኋላ አላለችም።
የኾነው ኾኖ ያቺ በቀይ ባሕር ላይ የሠለጠነችው ኢትዮጵያ ዛሬም ድረስ በደሟ ውስጥ ታላቅነት በጉልህ ይንጸባረቃል። የባሕር በር አልባነት የትውልድ የቤት ሥራ ኾኖም መጥቷል። ታላቋ ሀገር ኢትዮጵያ ሥልጣኔዋ፣ እድገቷ እና ኀያልነቷ በዚህ አሳዛኝ መገለል ተቋጭቶ ይቀራልን? ሲባሉም ምላሻቸው “በፍጹም” የሚል ኾኗል።
በርግጥስ በአንድ ወቅት የአሸባሪዎች ምስ፤ የተበዳዮች ዋስ የነበረችው ኢትዮጵያ በባሕር በር አልባነት የምትቀጥልበት ምን ዓይነት ታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ አመክንዮ ይኖራል ?
ኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር የምታደርገው ዳግም መመለስም የቀደመ ገናናነቷን የምታውጅበት የትንሣኤ ምዕራፍ ለመኾኑም ጥርጥር የለውም።እንደገና ወደ ባሕር በሯ ስትመለስ ያ የጥንቱ የንግድ ማዕከልነቷ እና የኢኮኖሚ ብልጽግናዋ እንደ አዲስ ያቆጠቁጣል። በራሷ መርከቦች የዓለምን ውቅያኖስ እየቀዘፈችም ኢኮኖሚዋን ትገነባለች። 🔥
ይህ ወደ ባሕር በር የመመለስ የኢትዮጵያ መሠረታዊ ጥያቄ ዕውን ሲሆን ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይኾን ለአፍሪካ ቀንድ ብሎም ለዓለም ንግድ አስተማማኝ የሰላም ዋስትና ኾና ታገለግላለች። ካሁኑ መደራጀት የጀመረው የባሕር ላይ ወታደራዊ ኀይሏ ግንባር ቀደም ሚና በሚጫወትበት አግባብ በጥንቱ ግርማዋ ልክ ዘመኑን የሚመጥን ኾኖ ይደራጃልና።💪
ለዚህም ነው የዲፕሎማሲና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህሩ እንዳለ ንጉሤ ከአሚኮ ጋር ባደረጉት ቆይታ “ኢትዮጵያ ወደ ባሕር በር ባለቤትነቷ በመመለሷ የሚጠቀም እንጅ የሚጎዳ አንዳች ዓለም የለም” ያሉት።
መምህሩ “በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ከባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በላይ ብሔራዊ ጥቅም የላትም” በማለት ትውልዱ ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጠው አስገንዝበዋል።
⚓ ታዲያ ይህ ትውልድ የታሪኩ ማደሻ የኾነውን ምዕራፍ በዝምታ ያስቀጥለዋል ወይስ የቀጣዩ ትውልድ መልሕቅ ይኾናል ? ውሳኔው የኹላችንም ነው።
#አሚኮ_ዜና #ኢትዮጵያ #የባሕር_በር #SeaportForEthiopia #NationalInterest 🇪🇹 🚢 🛳️
#ባሕር_ዳር #ሐምሌ4_2018_ዓ_ም
በአድኖ ማርቆስ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
