
ባሕር ዳር፡ ሚያዝያ 01/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በአማራ ክልል እየተተገበረ ያለውን ነዳጅን በቁጠባ የመጠቀም ሥራ ተገን በማድረግ የሚከናወኑ ሕገ ወጥ ድርጊቶችን ለመቆጣጠር እና የትራንስፖርት አገልግሎቱን ለማረጋጋት የሚያስችል አዲስ ጥብቅ የአሠራር ሥርዓት መዘርጋቱን የክልሉ መንገድ፣ ትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ቢሮ አስታውቋል።
የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ
ቢሮ የትራንስፖርት አገልግሎት አቅርቦት ስምሪት ዳይሬክተር ጌታቸው መርሻ እንደገለጹት አዲሱ አሠራር በተለይ የከተማ ታክሲዎች እና ከከተማ ወደ ከተማ የሚንቀሳቀሱ የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች የቀዱትን ነዳጅ ለታለመለት የሕዝብ አገልግሎት ብቻ ማዋላቸውን ለማረጋገጥ ያለመ ነው።
ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ከቀዱ በኋላ ሥራ ከማከናወን ይልቅ ነዳጁን በጥቁር ገበያ የመሸጥ ዝንባሌ እንደሚታይባቸው መገምገሙን አስታውሰዋል። ይህንን ችግር ለመፍታት በኩፖን ላይ የተመሠረተ እና በእያንዳንዱ የጉዞ ዙር ላይ የሚያተኩር የቁጥጥር ስልት ተግባራዊ መደረጉን ተናግረዋል።
በዚህም መሠረት እያንዳንዱ ታክሲ በቀን ውስጥ ያከናወነው የጉዞ ብዛት ከመነሻ እና መድረሻ ጣቢያዎች አልፎ በየፌርማታው ባሉ የስምሪት ሠራተኞች አማካኝነት በየሰዓቱ ይመዘገባል። ይህም ነዳጅ በአግባቡ ሥራ ላይ እየዋለ መኾኑን ለማረጋገጥ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በባሕር ዳር ከተማ የሚገኙ ዘጠኝ የሕዝብ ትራንስፖርት ማኅበራትም በስምሪት በሠራተኞቻቸው አማካኝነት የኮድ ሦሥት ተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴ በቅርበት እንዲከታተሉ ኀላፊነት ተሰጥቷቸዋል። ይህ የተቀናጀ አሠራር ነዳጅ ቀድተው ከሥራ መስክ የሚሰወሩ ተሽከርካሪዎችን በቀላሉ ለመለየት እና እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ነው ብለዋል።
ሥራውን ውጤታማ ለማድረግም ቢሮው ከክልሉ ንግድ እና ገበያ ልማት ቢሮ እና ከነዳጅ አቅርቦት ኮሚቴ ጋር በቅንጅት እየሠራ መኾኑን አስታውቋል።
ዘጋቢ፦ስማቸው አጥናፍ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
