
ባሕር ዳር: መጋቢት28/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ ከባንኮች እና ከፋይናንስ ተቋማት ጋር መተሳሰሩ በዘርፉ ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎችን ይዞ ብቅ ብሏል።
ከዚህ ቀደም ባንኮች የአንድን ደንበኛ ማንነት ለማረጋገጥ “ደንበኛህን እወቅ” (Know Your Customer – KYC) ተብሎ የሚጠራው በጽሑፍ መልዕክቶች ማንነት የማረጋገጥ ሂደት ወጭ እና ጊዜ ያባክን ነበር።
በብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጽሕፈት ቤት የምዝገባ አሥተባባሪ ደጀኔ ገብሬ አኹን በፋይዳ መታወቂያ አማካኝነት ወደ ዲጂታል ማንነት ማረጋገጫ ወይንም ኤሌክትሮኒክ ዘዴ ደንበኛን ማወቅ (Electronically Know Your Customer – eKYC) መቀየሩን ገልጸዋል።
ይህ ደግሞ፦
#ደንበኞችም ማንነታቸውን ለማረጋገጥ እና አገልግሎት ለማግኘት የሚያወጡትን የሃብት እና የጊዜ ብክነት ይከላከላል። ይህ ደግሞ በባንክ እና በደንበኞች መካከል ጥብቅ ትውውቅ እና መተማመን እንዲኖር ያደርጋል ብለዋል።
#ከዚህም ባሻገር በፋይናንስ ሥርዓቱ ውስጥ የሚታዩ የማጭበርበር ድርጊቶችን እና ማንነታቸው የማይታወቅ የባንክ ሂሳቦችን ለማስቀረት አቅም ይፈጥራል። ይህ ደግሞ እንደ ሀገር የምጣኔ ሃብት እንቅስቃሴን የማነቃቃት አቅም ያሳድጋል።
አሁን ላይ ማኅበረሰቡ በኦንላይን እና በአካል በመገኘት የፋይዳ መታወቂያውን ከባንክ ሂሳቡ ጋር የማስተሳሰር ሥራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። ማኅበረሰቡ ይህንን አጠናክሮ እንዲቀጥልም አሥተባባሪው አሳስበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
