
ባሕር ዳር: መጋቢት 21/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ደም መለገስ አንድ ጤነኛ ሰው በፍላጎት ወይም በፈቃደኝነት ላይ ተመሥርቶ የሚያደረገው በጎ ተግባር ነው፡፡ ይህም ከስጦታዎች ሁሉ የላቀ ሕይወት አድን ስጦታ ነው ማለት ይቻላል።
መጋቢት ወር የደም ልገሳ ወር ተብሎ ከበርካታ ደጋጎች ደም ይሠበሠባል። አሚኮ ዲጂታል ሚዲያም ወሩን ለማስታወስ 44 ጊዜ ደም የለገሱ አንድ ባለ ታሪክ አነጋግሯል።
የባሕር ዳር ከተማ ነዋሪ የኾኑት ፍሬሕይወት ሙስጦፋ በዚህ ዘርፍ የሚመሰገኑ ናቸው። በደም እጥረት ምክንያት የሚታጣውን ሕይወት ለመታደግም በበጎ ፈቃድ 44 ጊዜ ደም ለግሰዋል። ደሜን አልሰጥም የሚል የግንዛቤ ክፍተት በነበርበት ወቅት ደም የለገሱበትን አጋጣሚ ወደኋላ ተመልሰው አስታውሰዋል። ወቅቱ 2006 ዓ.ም ነበር። ለበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወደ ሆስፒታል ያመራሉ። ከሆስፒታሉ አንዲት ከገጠር የመጣች ወላድ እናት ደም ፈሰሳት እና የደም እጥረት አጋጠማት ይላሉ።
በወቅቱ ደም ከቤተሠብ ይወሰድ ነበር፤ ነገር ግን በዙሪያዋ የነበሩ ሰዋች ደም ለመስጠት አልቻሉም ነው ያሉት። ያንጊዜ ለምን ደም አልሰጣትም እና ለሕይወቷ መዳን ምክንያት አልኾንም ብዬ ጀመርኩ ነው ያሉት።
ምግብ እንኳ በደንብ አልተመገብኩም ነበር የሚሉት ባለታሪካችን ከፈጣሪ በታች ለሕይወቷ መዳን ምክንያት በመኾኔ በቃላት የማይገለጽ የህሊና ስንቅ አግኝቻለሁ ብለዋል።
“ሰው ለሰው መድኃኒት ነው” የሚሉት ባለ ታሪካችን በአጋጣሚ በመልካም ስብዕና የጀመሩት የደም ልገሳ በዓመት ሦስት ጊዜ በመለገስ አሁን ላይ 44 ጊዜ ደርሰዋል።
ደም በመለገሳቸው በጤናቸው ላይ ምንም ተጵዕኖ እንደሌለውም ገልጸውልናል። የህሊና እርካታ ይሰጣል ነው ያሉት። ደም መለገስን እንደ ባሕል እና አኗኗር ዘዴ ማድረጋቸውን የተናገሩት ባለ ታሪካችን “ደም አለመለገስ መድኃኒት ይዞ አልሰጥም እንደማለት ይቆጠራል” ብለዋል።
ደም መለገስ ቅዱስ ተግባር በመኾኑ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል።
ኅብረተሰቡ የእርሳቸውን ተሞክሮ በመከተል በየሦስት ወሩ በቋሚነት የደም ልገሳን ባሕሉ በማድረግ የወገኖቹን ሕይወት እንዲታደግ ጥሪ አቅርበዋል።
ለመኾኑ ስንቶቻችን ደም ለግሰን የደም እጥረት ለገጠማቸው ሰዎች ደርሰናል ?
ዘጋቢ፦ ሥራውድንቅ ደሳለው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
