
ባሕር ዳር: መጋቢት 08/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በሰሜን ሸዋ ዞን የባሶና ወራና፣ የአንጎለላ ጣራ ወረዳ እና የቡልጋ ከተማ አሥተዳደር የሰላም፣ ልማት እና የወቅታዊ ተግባራት ሁኔታ የግምገማ መድረክ ተካሂዷል።
በመድረኩ የተገኙት በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አሥተባባሪ አሕመዲን መሐመድ (ዶ.ር) በቀሪ ወራት መደበኛ የልማት እና የኢኒሼቲቨ ሥራዎች በተገቢው መንገድ እንዲፈጸሙ አልቆ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።
የአገልግሎት አሰጣጥን መፈተሽ እና በየደረጃው ያለውን የሕዝብ አንገብጋቢ የኾኑ ጥያቄዎች የመመለስ ሥራ የዘወትር ተግባር መኾን እንዳለበትም ገልጸዋል።
“ሕዝብ እንደ ባለቤት ሲሳተፍ ሰላም ይጸናል” ያሉት ዶክተር አሕመዲን ሕዝቡ የሰላሙ ባለቤት እንዲኾን ለማስቻል በየደረጃው ከሚገኙ የማኅበረሰብ ክፍሎች ጋር ውይይትን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።
7ኛው ሀገራዊ እና ክልላዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊ እንዲኾን እንዲሁም የምርጫ ጣቢያዎች ያለ ምንም የጸጥታ ስጋት እንዲሠሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ይገባል ነው ያሉት። ከፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ጋርም በቅንጅት መሥራት እንደሚያስፈልግ መናገራቸውን ከሰሜን ሸዋ ዞን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
