
አዲስ አበባ: መጋቢት 06/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የሲዳማ ሕዝብ የዘመን መለወጫ በዓል ፊቼ ጫምባላላ በሀዋሳ ሶሬሳ ጉዱ ማሌ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
ፊቼ ጫምባላላ የሲዳማ ሕዝብ የራሱን ዘመን የሚለውጥበት ደማቅ በዓል ነው።
በበዓሉ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የሲዳማ ክልል ርእሰ መሥተዳድር ደስታ ሌዳሞ ፊቼ ደግሶ አብሮ የመብላት እና የመጠጣት ሥርዓት ነው ብለዋል። ይህም ያለ አድሎ የሚከወን በመኾኑ የአብሮነት ምሳሌ ተደርጎ ይወሰዳል ነው ያሉት።
በዓሉ ሰው ብቻ ሳይኾን እንስሳቱ ሁሉ በነጻነት የሚውሉበት መኾኑንም አንስተዋል። “ጫምባላላ ለሰላም የሚጸለይበት፣ ቁርሾ እና ጥላቻ የሚወገድበት ሥርዓት ነውም” ብለዋል ።
ፊቼ ጫምባላላ የሰላም በዓል እንደመኾኑ ዓለማችን መነጋገር እና መተሳሰብ አቅቷት በጦርነት እየታመሰች ባለችበት በዚህ ወቅት ለሀገራችን እና ለዓለም ሰላምን ይሰብካል ነው ያሉት።
በመደመር፣ በመነጋገር እና ውይይትን በማስቀደም ለአብሮነት እና ለሰላም ልንቆም ይገባልም ብለዋል።
ዘጋቢ፦ ድልነሳ መንግሥቴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
