
ባሕር ዳር፡ ጥር 29/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በኢትዮጵያ የቱርክዬ አምባሳደር በርክ ባራን ከአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አለምአንተ አግደው ጋር በፍትሕ ሥርዓት ማሻሻያ እና በጋራ በሚሠሩ ጉዳዮች ላይ ውጤታማ ውይይት አድርገዋል።
የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የዳኝነት አገልግሎቱን በመሠረታዊነት ለማሻሻል ስርነቀል የለውጥ ሂደት ላይ እንደሚገኝ በውይይቱ ተመላክቷል።
የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ዓለምአንተ አግደው ፍርድ ቤቱ የኅብረተሰቡን አመኔታ ያረጋገጠ ለማድረግ ሥራዎች እየተሠሩ መኾኑን ገልጸዋል።
ተምሳሌት የኾነ ፍርድ ቤት ለመገንባት እና የቴክኖሎጂ ተደራሽነትን በማረጋገጥ ዘመናዊ የዳኝነት መስጫ ማዕከል የማድረግ ተግባራት ስለመከናወናቸውም አስገንዝበዋል።
አማራጭ የሙግት መፍቻ ሥርዓቶችን በማጠናከር፣ በተለይም የባሕላዊ ፍርድ ቤቶች ዕውቅና እና አደረጃጀት ላይ ትኩረት በመስጠት ሥራ እንደተሠራም አስገንዝበዋል።
በሰው ኀይል አቅም ግንባታ ላይ የሚከናወኑ ሁሉን አቀፍ የማሻሻያ ሥራዎችም እየተከናወኑ ስለመኾናቸው አብራርተዋል።
የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንቱ አምባሳደሩ ለዕቅዶቹ የሰጡትን ትኩረት እና በጋራ ለመሥራት ያሳዩትን ፍላጎት አድንቀው አመሥግነዋል። አክለውም አምባሳደሩ በክልሉ ፍትሕ ሥርዓት ውስጥ አሻራቸውን እንዲያሳርፉ እና የዚህ ታሪካዊ የለውጥ ጉዞ አካል እንዲኾኑም ጥሪ አቅርበዋል።
በውይይቱ የቱርክዬ አምባሳደር በርክ ባራን ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ እየሠራቸው ያሉ የለውጥ ተግባራት እና የተቀመጡ ግልጽ ዕቅዶች እንዳስገረሟቸው ገልጸዋል።
አምባሳደሩ ፍርድ ቤቱ የያዘውን ርዕይ ለማሳካት በሚያደርገው ጉዞ ውስጥ ሀገራቸው አስፈላጊውን እገዛ እና ትብብር ለማድረግ ዝግጁ መኾኗንም አረጋግጠዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
