
ባሕር ዳር: ጥር 28/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ምክር ቤት በ6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን፣ 11ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ አዲስ የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ማጽደቁ ይታወቃል፡፡
ይህ አዋጅ ምን አዲስ ነገር ይዞ መጥቷል?
በአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ተጠሪ ዳኛ ስለሽ አብርሐም በአዲስ የወጡትን የፌዴራል የመንግሥት አገልግሎት እና አሥተዳደር ፖሊሲ እና የፌዴራል የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 1353/2017 ለማስፈጸም አዋጁ መውጣቱን ተናግረዋል።
ነባሩ የአማራ ክልል የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 253/2010 ሙሉ ባለመኾኑ አዲሱ አዋጅ መዘጋጀቱን አንስተዋል፡፡
አዋጁ 16 ክፍሎች እና 151 አንቀጾች ያሉት ሲኾን በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ሲወጣ ቁጥር እንደሚሰጠው ጠቁመዋል፡፡ አዲሱ የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ይዟቸው የመጡ አዳዲስ ጉዳዮችንም ባለሙያው አብራርተዋል፡፡
👉 የአዋጁ የተፈጻሚነት ወሰኑ ከነባሩ የመንግሥት ሠራተኛ እና ተቋማት በተጨማሪ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ተፈጻሚ ይኾናል ብለዋል።
👉 መሥሪያ ቤቶች እና ሠራተኞች ተግባራትን ሲያከናውኑ የሥራ ባሕል እና የሥራ አመራርን ተከትሎ መኾን እንዳለበት እሴቶችን ጥሏል።
👉 ከመንግሥት መሥሪያ ቤት መዋቅራዊ አደረጃጀት ጋር የሕዝብ ብዛት፣ የሚሰበሰብ ገቢ፣ የቆዳ ስፋት፣ ቁጥጥር የሚደረግበት እና ከፌዴራል ተቋማት ጋር የተናበበ መኾን እንዳለበት፤
👉 የደመወዝ ስኬል በፌዴራል ደረጃ በየአራት ዓመቱ የሚወሰነው የሥራ ደረጃ መነሻ ዝቅተኛ ደመወዝ እና ከፍተኛ ጣሪያ ደመወዝ በክልሉ ተግባራዊ እንደሚደረግ፤
👉 ከደመወዝ ጭማሪ ጋር በተያያዘ ሜሪት እና የደመወዝ ቦርድ ይቋቋማል፡፡ ቦርዱም ሀገራዊ የመክፈል አቅምን መሰረት በማድረግ በየጊዜው የሚከሰተውን የኑሮ ውድነት ለመቋቋም የሚያግዝ የደመወዝ ጭማሪ ያደርጋል ነው ያሉት።
👉 የመንግሥት አገልግሎቱን ውጤታማ ለማድረግ እያንዳንዱ ሥራ ላይ እና አዲስ ሠራተኛም የብቃት ምዘና ፈተና ይፈተናል፡፡
የሚቋቋመው የብቃት ምዘና ማዕከል ሠራተኞችን የብቃት ምዘና በመፈተን የሚያልፉት ወደ ሥራ ይገባሉ፤ ያላለፉትን ደግሞ የማሟያ ሥልጠና በመስጠት እንዲበቁ ያደርጋል ብለዋል፡፡
ሥልጠና ወስደው ለተከታታይ ሁለት ጊዜ የማለፊያ ነጥብ ካላመጡ ከመንግሥት ሥራ እንደሚሰናበቱ ተቀምጧል ነው ያሉት፡፡
👉 የብቃት ምዘናን ማለፍ ያልቻሉ ሠራተኞችን በሚመለከት ለጡረታ ዕድሜያቸው ያልደረሱ እና ከ25 ዓመት በታች ያገለገሉ ሁለት ዓመት የተጣራ ደመወዝ በአንድ ጊዜ ተከፍሏቸው ከሥራ ይሰናበታሉ፡፡ 25 ዓመት አገልግለው ዕድሜያቸው ከ50 እስከ 55 ለኾኑ ሠራተኞች ጡረታ የሚወጡበትን ሁኔታ አመቻችቷል ብለዋል፡፡
👉 የመንግሥት መሥሪያ ቤት አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን የአንድ ማዕከል ሥርዓት የመዘርጋት ግዴታ ተቀምጧል ብለዋል፡፡
👉 ሁኔታዎች ሲያስገድዱ ብቃትን መሠረት በማድረግ አንድን የመንግሥት ሠራተኛ ከአንድ ዓመት ላልበለጠ ጊዜ ከፍ ያለ የሥራ መደብ ላይ በተጠባባቂነት እንዲሠራ ማድረግ ይቻላል፡፡
በፊት በውክልና ጥቅም ሳያገኝ ይሠራ ነበር፤ አሁን ግን በተጠባባቂነት ሢሠራ የተጠባባቂነት አበል እንደሚከፈለው እና ተጠያቂነትም ጭምር ተቀምጧል ነው ያሉት።
👉 የመደበኛ የሥራ ሰዓት በፊት በሳምንት 39 ሰዓት የነበረው አስፈላጊ ኾኖ በተገኘ ጊዜ የአንድ መንግሥት ሠራተኛ በሳምንት ከ39 ሰዓት ሳያንስ እና ከ48 ሰዓት ሳይበልጥ ይኾናል፤
👉 አንድ እናት ከሦስት ወር ያልበለጠ ሕጻን ልጅ ለማሳደግ በጉዲፍቻ ከተረከበች የሦስት ወር እንደ ወሊድ ፈቃድ እንዲሰጥ ፈቅዷል፤
👉 በሥራ ላይ በአደጋ ምክንያት ለሚከሰት ሞት ለቤተሰቦቹ የአንድ ዓመት ደመወዝ እንደሚከፈል ተቀምጧል፤
👉 መሥሪያ ቤቶች የሠራተኞችን ዲጂታል የመረጃ ቋት ማደራጀት አለበት፤ ይህም በተለያየ ምክንያት በሚፈጠር ችግር የሠራተኞችን ማኅደር ለመጠበቅ የታሰበ ነው፡፡
👉 ኦዲት እና ኢንስፔክሽን ላይ የመንግሥት ተቋማት አገልግሎቱን በሕግ ስለመሠራቱ የማረጋገጥ ሥራ እንደሚሠራ አዋጁ በአዲስ ያካተታቸው ጉዳዮች ናቸው ብለዋል።
ለአዋጁ ማሥፈጸሚያ ደንብ እና መመሪያዎች እንደሚወጡም ተናግረዋል፡፡
ዘጋቢ፦ ፍሬሕይወት አዘዘው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
