
ደሴ: ጥር 04/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የደቡብ ወሎ ዞን እና የደሴ ከተማ አሥተዳደር የባሕል ፍርድ ቤቶች የማስጀመሪያ መርሐግብር በደሴ ከተማ እየተካሄደ ነው።
የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ዓለምአንተ አግደው የባሕላዊ ፍርድ ቤቶች የማስጀመሪያ ሥነ ሥርዓት ከባሕር ዳር በመቀጠል በደሴ ከተማ እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የዳበረ የሀገር በቀል ዕውቀቶች ባለቤት መኾኗንም አመላክተዋል።
የአማራ ክልል በሀገር በቀል ዕውቀቶች የዳበረ ባሕል አለው ያሉት ፕሬዝዳንቱ ይህ ሀገር በቀል ዕውቀት በስፋት ከሚተገበርባቸው አካባቢዎችም አንዱ ወሎ እና አካባቢው መኾኑንም አንስተዋል።
ሀገር በቀል ዕውቀቶች ለማኀበረሰቡ ሰፊ አገልግሎት እየሰጡ ቢኾንም የሕግ ማዕቀፍ እንዳልነበራቸው ገልጸዋል።
ላለፉት 30 ዓመታት ፋይዳቸውን ከመግለጽ ባሻገር ዝርዝር መመሪያም እንዳልነበራቸውም አንስተዋል።
የባሕል ፍርድ ቤት የሚከወነው በፈቃደኝነት ላይ ተመስርቶ መኾኑን ያነሱት ፕሬዝዳንቱ የፍርድ ሥርዓቱ ዘላቂ ሰላምን ከማረጋገጡ ባሻገር የዜጎችን እንግልት ይቀንሳል ብለዋል።
ለባሕል ሕጉ ተፈፃሚነት መንግሥት በልዩ ትኩረት እየሠራ መኾኑንም ገልጸዋል። ለተፈፃሚነቱ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ኀላፊነታቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል።
ዘጋቢ:- አበሻ አንለይ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
