
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 28/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አሥተላልፈዋል።
ርእሠ መሥተዳድሩ በማኀበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ ብለዋል።
በክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በየዓመቱ በድምቀት ከሚከበሩት በዓላት መካከል አንዱ የልደት በዓል መኾኑን ገልጸዋል። የልደት በዓል ጨለማ በብርሃን፤ ሞት በሕይወት የተሸነፈበት የድል ቀን ነው። በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ፍጹም እርቅ ወርዶ ፍቅር የነገሰበት ታላቅ የደስታ ቀን ነው ብለዋል።
ይህ በዓል የሃይማኖታዊ እሴቶቻችን መገለጫ ብቻ ሳይኾን እጅ ለእጅ ተያይዘን የምንረዳዳበት የምግባር መድረክ ነው። ውብ ባሕላችንን ተንከባክበን ለቀጣዩ ትውልድ የማሳለፍ አደራ የሁላችንም ነው።
በዓሉን ስናከብር ያለን ለሌላቸው በማካፈል እና የተቸገሩ ወገኖቻችንን በመርዳት ሊኾን ይገባል። ለሃይማኖቱ ተከታዮች በሙሉ በዓሉ የሰላምና የደስታ እንዲሆን እመኛለሁ ብለዋል በመልዕክታቸው።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
