
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 24/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) በኅዳር እና ታኅሣሥ ወር 2018 ዓ.ም ቁልፍ የኾኑ ተከታታይ ሀገራዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ተግባራትን አከናውነዋል።
ሁሉም ክንውኖች የኢትዮጵያን ተፈላጊነት እና ተጽዕኖ ፈጣሪነት በጽኖ መሠረት ላይ ያስቀመጡ ናቸው። የህንድ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውን ተከትሎ፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ያካሄዱት የሁለትዮሽ ውይይት እና በሀገራቱ መካከል የተደረሰው ሁሉን አቀፍ ስምምነት ትልቅ ትርጉም ተሰጥቶታል።
የመሪዎቹ ውይይት በዋናነት በንግድ እና ኢንቬስትመንት፣ በዲጂታይዜሽን እና ቱሪዝም ያለውን ትብብር በኢትዮጵያ እና ህንድ መካከል ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ያለመ ነው። በተጨማሪም በሁለቱ ሀገራት መካከል በጉምሩክ የጋራ አሥተዳደር ድጋፍ፣ በኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዳታ ማዕከል ምሥረታ የመግባቢያ ሥምምነቶች፣ በዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ላይ ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እና የሚያጠናክር የተባበሩት መንግሥታት የሰላም ማስከበር ሥራ የመግባቢያ ሥምምነት ፊርማ የተከናወነበት ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) እና ጠቅላይ ሚኒስትር ሞዲ በፓርላማ ተገኝተው የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር በየኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች እና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ ላይ ንግግር አድርገዋል።
አህጉራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ከአፍሪካ እና ቀጣናዊ አጋሮች ጋር በመገናኘት ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ክላቨር ጋቴቴ ጋር እ.ኤ.አ በ2027 አፍሪካን በሚገባ የሚወክል ኮፕ 32 በማዘጋጀት ረገድ ከኢትዮጵያ ጋር በጋራ ስለሚሰሩባቸው መንገዶች ውይይት አካሂደዋል።
በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ኅብረት አህጉሪቱን በሚገባ የሚወክል ጉባኤ ለማዘጋጀት እንዴት ተቀራርበው መሥራት እንደሚችሉ አስቻይ ሁኔታዎችን ለመፍጠር፥ ከአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር እና ከቡድናቸው ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱም ኮፕ 32ን (COP32) የተሳካ ለማድረግ የኢትዮጵያ ቁልፍ አጋርነት እና አፍሪካዊ መፍትሔ ስለሚጠናከርበት መንገድ ተነስቷል።
በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የሶማሊያ ፌደራል ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼኽ መሐሙድን እና የኬንያውን ፕሬዝዳንት ዊልያም ሩቶን ለሥራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ በመጡበት ወቅት ተቀብለው አነጋግረዋል። ከሁለቱ መሪዎች ጋር የነበረው ውይይት በዋናነት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች በሚጠናከርበት ሁኔታ ላይ ያጠነጠነ ነበር። በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ መሪዎቹ ሃሳብ ተለዋውጠዋል። ይኽም በሰላም እና መረጋጋት፣ ንግግር ብሎም በአፍሪካ መር መፍትሔዎች ላይ ያላቸውን የወል ጽኑ አቋም አጽንኦት የሰጠ ነበር።
በሀገር ውስጥ ጉዳዮች ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የታለመለትን ግብ አሳክቶ በመጠናቀቁ፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 በይፋ አስጀምረዋል። ይህ ስትራቴጂክ ፕሮግራም ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠር፣ በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ቁልፍ እና መሰረታዊ ትልሞቹ ኾኖ ወደ ትግበራ ገብቷል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 በተለይ የሕዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማትን ማስፋት ላይ ትልቅ ሥራ የሚከናወን ነው። ይህም ዲጂታል ቴክኖሎጂ ሰው ተኮር ኾኖ የዜጎችን ኑሮ እንዲያሻሽል ትልቅ አቅም ይፈጥራል።
በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደገለጹት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የተቀመጡ ግቦች እንዲሳኩ ሁለት መሠረታዊ አስቻይ ጉዳዮች እንዳሉ ጠቁመዋል። አንደኛው የኤሌክትሪክ ተደራሽነት ነው። የኤሌክትሪክ ተደራሽነት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ምግብ ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል ብለዋል። ሁለተኛው ደግሞ የኢንተርኔት ትስስር ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በርካታ ከተሞች የኢንተርኔት ትስስር ተጠቃሚ እንደኾኑ ተናገረዋል። ነገር ግን በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ይህን ትስስር በሁሉም አካባቢዎች ሙሉ ለሙሉ ተደራሽ ማድረግ እንዳለበትም አጽንኦት ሰጥተዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የሞባይል ተጠቃሚ ደንበኞች ቁጥር 128 ሚሊዮን ይደርሳል። የ5ጂ ኔትወርክ ሽፋንን 100 ከተሞች እንደሚደርስ ይጠበቃል።
በአጠቃላይ በዲጂታል ኢትዮጵያ የሚከናወኑ ሥራዎች የመደመር መንግሥት በቀለለ ቢሮክራሲ ታላላቅ ስትራቴጂዎችን እውን ለማድረግ ከያዘው ግብ ጋር የተሳሰሩ ናቸው ብለዋል።
በሌላ በኩል የ20ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በዓል በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በውቢቱ ሆሳዕና ከተማ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች በተገኙበት በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በበዓሉ ባደረጉት ንግግር “የኢትዮጵያን ችግሮች ብቻ ሳይኾን አቅሞቿን መመልከት ይገባናል” ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፥ “አንድ ክር ደካማ ነው፤ ብዙ ክር ግን የማይበጠስ ገመድ ይፈጥራል። ስንበዛና ስንሰናሰል በቀላሉ የማንበጠስ ስለምንሆን፤ መተባበር፣ በጋራ መቆምና ብሔራዊ ጥቅም ማስከበር የሁላችን ስንቅ ሊሆን ይገባል ነው ያሉት። በሚቀጥለው ዓመትም የጅማ ከተማ 21ኛውን በዓል እንደምታከብርም በፕሮግራሙ ላይ ተገልጿል።
በኅዳር እና ታኅሣሥ ወር የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) አመራር ኢትዮጵያ በሀገር ውስጥ ዘመናዊነትን በማሳለጥ፤ በአህጉር እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ስትራቴጂካዊ ዲፕሎማሲዋን በማጠናክር ረገድ ያላትን ቁረጠኝነት ያረጋገጠችበት ነው።
ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው በዚህም የዲጂታል አካታችነትን በማጎልበት፣ ቀጠናዊ አጋርነትን በማሳደግ እና ዓለም አቀፍ ትብብርን በማጠናከር፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፋዊ ከፍተዋን አጽንታለች።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
