
አዲስ አበባ: ታኅሣሥ 23/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር እና ተጠሪ ተቋማት ሪፎርም ሊያካሂድ መኾኑን አስታውቀዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ በተቋማት ሪፎርም እየተካሄደ ነው። የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በሁለተኛ ዙር የመንግሥት አገልግሎት እና አሥተዳደር ሪፎርም ተግባራዊ እንዲያደርጉ ከተመረጡ መሥሪያ ቤቶች ውስጥም አንዱ ነው።
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱም ሪፎርሙን ተግባራዊ ለማድረግ ኮሚቴ አቋቁሞ ወደ ሥራ ገብቷል።
ሪፎርሙን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችለውን ስምምነት ከከፍተኛ የትምህርት እና ሥልጠና ተቋማት ጋር ፈጽሟል።
የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ሪፎርሙ ጠንካራ፣ በወቅቶች እና በሁኔታዎች የማይበገር ተቋም መመስረትን ዓላማ ያደረገ መኾኑን አስታውቀዋል።
ሪፎርሙ ሰፋ ሰፊ እና ሰባት የሪፎርም አምዶችን አካትቷል ተብሏል። በሪፎርሙ ተቋምን ማዘመን እና ሠራተኞችን ማብቃት ላይ ትኩረት እንደሚደረግም ነው የተብራራው።
በሰው ኀይል በኩል የሚደረገው ሪፎርም ለሠራተኞች የብቃት ፈተና በማዘጋጀት እንደሚሰጥ እና ፈተናውን ያለፉ ሠራተኞች ምደባ እንደሚካሄድ ገልጸዋል።
ምዘናውን ያላለፉ ሠራተኞች ሥልጠና ወስደው መብቃታቸው ሲረጋገጥ ምደባው እንደሚካሄድም ተነስቷል።
ዘጋቢ፦ተመስገን ዳረጎት
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
