
ባሕርዳር፡ ታኅሣሥ 09/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ገቢዎች መምሪያ የአምስት ወራት የገቢ አፈጻጸሙን እየገመገመ ነው። በግምገማው የከተማ አሥተዳደሩ እና የክፍለ ከተማ የሥራ ኀላፊዎች እንዲኹም ሙያተኞች እየተሳተፋ ይገኛሉ።
የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው የዚህ በጀት ዓመት የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር የገቢ አሰባሰብ እቅድ ለከተማዋ ብቻ ሳይኾን ለአማራ ክልል የገቢ አሰባሰብ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መኾኑን ተናግረዋል።
ባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር በክልሉ ከፍተኛ ገቢ ከሚሰበሰብባቸው ከተሞች መካከል አንዷ ናት ያሉት ከንቲባው በየዓመቱ አዳጊ የኾነ የገቢ አሰባሰብ በከተማዋ እየታየ መኾኑን ነው የጠቀሱት።
የታቀደውን የገቢ አሰባሰብ እቅድ በአግባቡ መሰብሰብ ከተቻለም ክልሉን በገቢ አሰባሰብ ወደፊት ከፍ የሚያደርግ ሁኔታ ይፈጥራል ነው ያሉት።
በዚህ በጀት ዓመት በባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ለመሥራት በእቅድ የተያዙ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ሰፊ ሀብት የሚጠይቁ ናቸው፤ ይህን በአግባቡ መፈጸም የሚቻለው ደግሞ የተሻለ የገቢ አሰባሰብ ሲኖር ነው ብለዋል።
ከምርጫ በፊት ባሉ ጊዜዎችም የገቢ አሰባሰብን ጨምሮ በከተማ አሥተዳደሩ የታቀዱ ሌሎች እቅዶችን ለመፈጸም እየተሠራ እንደኾነ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፦ ሮዛ የሻነህ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
