
አዲስ አበባ: ታኅሣሥ 03/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ሀገር አቀፍ የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ማሥጀመሪያ መርሐ ግብር በሐዋሳ ከተማ ተካሂዷል።
ነርቭን በማጥቃት ሕጻናትን ለአካል ጉዳት የሚዳርገው የፖሊዮ ቫይረስ ትልቁ እና አንዱ የዓለም አጀንዳ ነው። እንደ ዘርፉ ባለሙያዎች መረጃ ሦስት ዓይነት የፖሊዮ ቫይረሶች የተለዩ ሲኾን እስካሁን ሁለቱን በተደረገው የክትባት ርብርብ ማጥፋት ተችሏል።
በማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትሯ መቅደስ ዳባ (ዶ.ር) በዚህ መርሐ ግብር ከ24 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የኾኑ ሕጻናት ተደራሽ ይደረጋሉ ብለዋል።
ክትባቱ ቤት ለቤት እንደሚሰጥ የገለጹት ሚኒስትሯ ሕጻናቱ ከአሁን በፊት ቢከተቡም ባይከተቡም ክትባቱን እንደሚወስዱ ነው የተናገሩት።
በክትባቱ ወቅት የማርበርግ ቫይረስ ቅኝት እንደሚደረግ የገለጹት ሚኒስትሯ ቤት ውስጥ ህመም ገጥሟቸው ያለ ሕክምና የተቀመጡ ዜጎችም አገልግሎት ያገኛሉ ብለዋል። የጤና ግንዛቤ ትምህርትም ይሰጣል ነው ያሉት።
ጤናማ ዜጋ በመፍጠር ሂደት የሁሉም ኀላፊነት በመኾኑ የጤና ባለሙያዎችን ለክትባት ሲመጡ ቀና ትብብር እንዲያደርግላቸውም ጥሪ አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ:- በለጠ ታረቀኝ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
