
አዲስ አበባ: ኅዳር 02/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የኢፌዴሪ አየር ኀይል 90ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን አስመልክቶ የስፖርት ፌስቲቫል እያካሄደ ነው።
የኢፌዴሪ አየር ኀይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ ሠራዊቱ እና ስፖርት ጥብቅ ትስስር አላቸው ብለዋል። በሥልጠና እና የበረራ ትጥቅን በማሻሻል ጠንካራ አየር ኀይል የመገንባት ተግባሩ ተጠናክሮ ቀጥሏል ነው ያሉት።
ሠራዊቱ አካላዊ ብቃቱ የተስተካከለ እና ተልዕኮውን በብቃት የሚወጣ ለማድረግ ስፖርት ዘወትራዊ ተግባር ነው ብለዋል።
ይህ ስፖርታዊ ውድድር ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ዕድል ኾኖ እንደሚያገለግልም አመላክተዋል።
የአየር ኀይል ስታፍ አስተባባሪ ብርጋዴል ጄኔራል አበበ ተካ ከአየር ኀይል የምሥረታ በዓል መርሐ ግብር አንዱ የኾነው እና ዛሬ የተጀመረው የስፖርት ፌስቲቫል ለቀጣይ ሁለት ሳምንታት በተለያዩ የውድድር አይነቶች እንደሚካሄድ ገልጸዋል።
ስፖርታዊ ፌስቲቫሉ “ለአየር ኀይል ዕድገት በሙሉ አቅሜ እሮጣለሁ” በሚል መሪ መልዕክት ከሕዝብ እና ከጦር ክፍሎች በተውጣጡ ስፖርተኞች በቢሾፍቱ ከተማ በሚደረገው የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር እንደሚጠናቀቅም ተናግረዋል።
ዘጋቢ፦ ኢብራሂም ሙሐመድ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
